Saturday, July 9, 2016

የክብር ዶክትሬት በኛ ሀገር ክብሩን እንዲያጣ ተደርጎ እየተቀለደበት ነው ፡፡ (የዩኒቨርሲቲ ምሁራን)


የከፍተኛ ትምሕርት ተቋማት ምሁራኖች የዶክትሬት ዲግሪ ኣሰጣጥን በመተቸት ተቃወሙት።
Minilik Salsawi - mereja.com በሀገሪቱ ያሉ ዩኒቨርስቲዎች ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በየዓመቱ ለሁለትና ሶስት ሰዎች የክብር ዶክትሬት መስጠትን እንደ ልማድ መያዛቸው ከክብር ዶክትሬት መሰረታዊ አላማዎች ጋር የሚፃረርና ክብሩን የሚያራክስ ነው ሲሉ የዩኒቨርሲቲ ምሁራን ገለፁ፡፡የክብር ዶክትሬት የሚሰጥባቸው መስፈርቶች በመርፌ ቀዳዳ ግመል እንደ ማሽሎክ ያህል ናቸው ያሉት ምሁራኑ፤ በአሁን ወቅት አዳዲስ ዩኒቨርሲቲዎች ጭምር ፉክክር በሚመስል መልኩ ዶክትሬቱን የሚሰጡበት አካሄድ በአስቸኳይ ሊታረም እንደሚገባው አሳስበዋል፡፡

የክብር ዶክትሬቱ የተሰጠባቸው ግለሰቦችም ለስም መጠሪያነት መጠቀማቸው ተገቢ አይደለም ያሉት ምሁራኑ፤ መገናኛ ብዙኃን የክብር ዶክትሬት የተሰጠውን ግለሰብ፤ “የክብር ዶክተር” እያሉ መጥራታቸውም አግባብ ባለመሆኑ ማረም ይኖርባቸል ብለዋል፡፡የቋንቋና ስነ ፅሁፍ ምሁሩ ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ፤ ከሀገሪቱ ዩኒቨርሲቲዎች ለተለያዩ ግለሰቦች የክብር ዶክትሬት የሚሰጥበት ሁኔታ፤ ከማዕረጉ መሰረታዊ አላማ ጋር የተቃረነ መሆኑን አለማቀፍ ልምዶችን በማጣቀስ አስረድተዋል፡፡

በአሁን ወቅት በትምህርት በቅተዋል ተብለው ዶክትሬት ዲግሪ የሚሰጣቸው ምሁራን ምን ያህል ችግር ፈቺ ምርምር ሰርተዋል የሚለው ራሱ ጥያቄ ውስጥ እንደገባ የጠቆሙት ዶ/ር በድሉ፤ የክብር ዶክትሬት የሚሰጠው አንድ ግለሰብ ተምረው ዶክተር ከሆኑት ባልተናነሰ ሁኔታ ማህበረሰባዊ አስተዋፅኦ ሲያበረክትና ተፅዕኖ ፈጣሪ ሲሆን ብቻ ነው ብለዋል፡፡
“ማዕረጉ በመደበኛ ትምህርት ከሚገኘው ዶክትሬት ይበልጣል” ያሉት ምሁሩ፤ በዋናነት ከራሱ ማህበረሰብ ባለፈ ለዓለም ህብረተሰብ ያበረከተው አስተዋፅኦና በአለማቀፍ ደረጃ ያለው ተፅዕኖ ፈጣሪነት ከግምት ገብቶ ነው የክብር ዶክትሬቱ የሚሰጠው ብለዋል፡፡ “ማንም ሰው ከተማረ ዶክትሬቱን ያገኘዋል፤ ማንም ሰው ግን “የክብር ዶክትሬትን” ሊያገኝ አይችልም ያሉት ዶ/ር በድሉ፤ በኛ ሀገር ግን ክብሩን እንዲያጣ ተደርጎ እየተቀለደበት ነው ብለዋል፡፡
የክብር ዶክትሬት የሚሰጥባቸውን ዋነኛ መስፈርቶች የጠቆሙት ዶ/ሩ፤ ግለሰቡ ከትውልድ ሀገሩ አልፎ እንደ አትሌት ኃይሌ ገ/ስላሴ፣ አበበ ቢቂላ እንዲሁም ከአፍሪካ ህብረት ምስረታና ከሊግ ኦፍ ኔሽን ምስረታ ጋር ተያይዞ ስማቸው የሚነሳው አፄ ኃይለ ሥላሴ አይነት አለማቀፍ ተፅዕኖ ፈጣሪ ሲሆኑና ለአለም ያበረከቱት አስተዋፅኦ ለሌላው አርአያ ይሆናል ሲባል ብቻ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
በሀገራችን ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የተጀመረው አካሄድ ግን ወደ አካባቢ ተወላጅነትና ጎሳ እየወረደ መምጣቱን በመጥቀስ፤ ምን አስተዋፅኦ እንዳበረከቱ በጉልህ ያልተገመገሙ ግለሰቦች ጭምር እየተሰጣቸው መሆኑ የክብር ዶክትሬቱን ከአላማና መርህ ውጪ አድርጎታል ብለዋል፡፡ አብዛኞቹ የክብር ዶክትሬቱ የተሰጣቸው ግለሰቦች ይገባቸዋል የሚል እምነት እንደሌላቸው የጠቆሙት ምሁሩ፤ በሙዚቃው ዘርፍ ከጥላሁን ገሰሰና ከአስቴር አወቀ ውጪ ሌላ ይገባዋል ብዬ የምቀበለው ሰው የለም ብለዋል፡፡ የዶክትሬት ዲግሪ መርሃ ግብር የሌላቸው ዩኒቨርሲቲዎችም የክብር ዶክትሬት መስጠት እንደማይችሉ ዶ/ር በድሉ አስረግጠው ተናግረዋል፡፡

የዶ/ር በድሉን ሃሳብ የሚጋሩት የህግ ምሁሩ ፕሮፌሰር ጥላሁን ተሾመ በበኩላቸው፤ ጉዳዩ በእጅጉ አሳሳቢ ሆኗል ይላሉ፡፡ በሁለት መንገድ የክብር ዶክትሬት እንደሚሰጥ የጠቆሙት ፕ/ር ጥላሁን፤ በስነ ፅሁፍና በኪነ ጥበብ አለማቀፍ ተፅዕኖ የፈጠሩና በአገር አቀፍና በአለማቀፍ ደረጃ በተሰማሩበት ሙያ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ያደረጉ ሰዎች ናቸው ለማዕረጉ የሚመረጡት፡፡ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሴኔት ፀሐፊ ሆነው ማገልገላቸውን የሚያስታውሱት ፕ/ር ጥላሁን፤ በደርግ ዘመን የክብር ዶክትሬት መሰጠት ቆሞ እንደነበርና ዳግም ካስጀመሩት አንዱ መሆናቸውን ጠቅሰው፤ በስነ ፅሁፍ ለደራሲ ከበደ ሚካኤልና ኋላም ለደራሲ ሀዲስ አለማየሁ መሰጠቱን ያስታውሳሉ፡፡
የክብር ዶክትሬት የሚሰጠውን ግለሰብ ለመምረጥ ዩኒቨርሲቲዎች ብዙ እንደሚደክሙና ምናልባትም ለበርካት አመታት መስፈርቱን የሚያሟላ ግለሰብ ላይገኝ እንደሚችል የተናገሩት ፕ/ሩ፤ አሁን ላይ ዩኒቨርሲቲዎች ጉዳዩን የፉክክርና የባለስልጣናት እጅ መንሻ እያደረጉት ይመስላል ብለዋል፡፡ በአካባቢ ተወላጅነት መሆኑ ደግሞ ይበልጥ አሳሳቢ ያደርገዋል ያሉት ምሁሩ፤ ከሰሞኑ እየተሰጡ ያሉ የክብር ዶክትሬቶች ፖለቲካ ፖለቲካ የሚሸቱ መሆናቸውን ጠቁመው፤ ከፖለቲካ ነጻ የሆነ የክብር ዶክትሬት አሰጣጥ መስፈርት ሊኖር ይገባል ብለዋል፡፡ የክብር ዶክትሬት የተሰጣቸው ግለሰቦች ማዕረጉን ፈፅሞ ለመጠሪያነት ሊጠቀሙበት እንደማይገባ ሲናገሩም፤ “የክብር ዶክተርም” ሆነ “ክቡር ዶክተር” የሚለው አጠራር ፈፅሞ ስህተት ነው ብለዋል - ፕ/ር ጥላሁን፡፡
በንጉሡ ዘመን እንደ ሴኔጋሉ ፕሬዚዳንት ሴዳል ሴንጎር ላሉት የነፃነት ታጋዮች የክብር ዶክትሬቱ መሰጠቱን ያስታወሱት ምሁሩ፤ በወቅቱ ክብሩ ተጠብቆ እንዲቆይ እንደ ብርቅ ነበር የሚታየው፤ የአሁኑ አካሄድ ግን ልጓም ያጣ ሆኗል፤ በአስቸኳይ ሊስተካከልና ሊታረም ይገባል ሲሉ አሳስበዋል፡፡
ሌላው አስተያየታቸውን የሰጡት የፍልስፍና ምሁሩ ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ፤ ዩኒቨርሲቲ ማለት “ዩኒቨርሳል” ከሚለው ቃል እንደመሰየሙ አለማቀፍ ባህሪ እንጂ አካባቢያዊ ባህሪ እንደሌለው አውስተው፤ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ወደ ዘርና ጎሳ እየወረደ መምጣቱ ክብሩን አሳጥቶታል ብለዋል፡፡ ዩኒቨርሲቲ ለግለሰቡ ሲሰጥ ዩኒቨርሲቲውንም የሚያስከብር ይሆናል ያሉት ዶ/ር ዳኛቸው፤ ዩኒቨርሲቲዎቻችን አካባቢያዊ በመሆናቸው ከዚሁ የአካባቢያዊ ስሜት በመነጨ ለየአካባቢያቸው ተወላጆች ለመስጠት መሽቀዳደማቸው አሳፋሪ ነው ብለዋል፡፡ ከክብር ዶክትሬት አሰጣጥ አላማና መርህ ጋርም ፈፅሞ የሚሄድም አለመሆኑን ተናግረዋል፡፡addisadmassnews.com

No comments:

Post a Comment