Wednesday, August 12, 2015

በዘንድሮው ክረምት የተፈጠረው የዝናብ እጥረት አሉታዊ ተፅዕኖዎችን እያሳደረ ነው

11822387_10203331731012402_4786620687797120057_nለከብቶች መሞትና ለሰብል ውድመት ምክንያት ሆኗል

-ችግሩ አሳሳቢ በመሆኑ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚመራ ብሔራዊ ኮሚቴ ተቋቁሟል
x_lon_ethiopia_080805.video-260x195
በአገሪቱ አብዛኛዎቹ አካባቢዎች በዘንድሮው የክረምት ወቅት የተከሰተው የዝናብ እጥረት አሉታዊ ተፅዕኖዎችን እያሳደረ መምጣቱን፣ የብሔራዊ ሚቲዎሮሎጂ ኤጀንሲ ይፋ አደረገ፡፡
ዘግይቶ የመጣው የነሐሴ ዝናብ ሥርጭት መሻሻል እንደሚታይበት ገልጿል፡፡
ችግሩ ስለመከሰቱ ለመንግሥት ካሳወቀ ከሁለት ወራት በኋላ በይፋ በሰጠው መግለጫ የዝናብ እጥረቱ በአብዛኛው የአገሪቱ ክፍሎች መታየቱን ገልጾ፣ ይህም በእርሻ ሥራ አጀማመር፣ የዘር ጊዜን በማስተጓጎልና የሰብል ውኃ ፍላጎትን ባለማሟላትና በመሳሰሉት ተፅዕኖዎቸ እንዲጠናከሩ አድርጓል በማለት አስታውቋል፡፡
ነሐሴ 5 ቀን 2007 ዓ.ም. በኤጀንሲው የሥራ ኃላፊዎች በተሰጠው በዚሁ መግለጫ የዝናብ እጥረቱ ተፅዕኖ በሰብል ልማት ላይ ብቻ ሳይሆን፣ በተለይ በክረምት ወቅት በአገሪቱ ግድቦች መግባት የነበረበት ውኃ እንዲቀንስ ምክንያት መሆኑን አስታውቋል፡፡ የዝናብ እጥረት በየወንዞቹ የሚፈሰው ውኃ ዝቅ እንዲል፣ እንዲሁም በሜዳማና በረግረጋማ መሬት ላይ መተኛት የነበረበት የውኃ መጠን መቀነስ ጎልተው ከታዩ ክስተቶች ውስጥ እንደሚካተቱ ተጠቅሷል፡፡
የኤጀንሲው ዋና ዳይሬክተር አቶ ፈጠነ ተሾመ እንደገለጹት፣ በአብዛኛው የአገሪቱ ክፍል የታየው የዝናብ እጥረት በተለይ በሐምሌ ወር ጎልቶ ታይቷል፡፡ በሰኔ ወር የነበረው የዝናብ አጀማመር የተሻለ መጠንና ሥርጭት ቢኖረውም፣ በሐምሌ ግን የተዳከመ ገጽታ ስለነበረው በበርካታ የአገሪቱ አካባቢዎች ላይ ዝናብ እጥረት መከሰቱን፣ ይህም አሉታዊ ተፅዕኖዎች እንዳሳደረ ገልጸዋል፡፡
የዝናብ እጥረቱ ስላሳደረው ተፅዕኖ የኤጀንሲው ኃላፊዎች ዝርዝር ማብራሪያ ባይሰጡም፣ የዝናብ እጥረቱና የታየው ድርቅ ለሰብል መጥፋትና ለእንስሳት ሞት ምክንያት መሆኑን ከተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡ ከአፋር ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው በ31 ወረዳዎች ላይ ድርቅ ተከስቷል፡፡
በአንዳንድ ወረዳዎች እስከ 240 የሚደርሱ ፍየሎችና ግመሎች መሞታቸውን የሚያሳዩ መረጃዎች እንደደረሰም የክልሉ ኮሙዩኒኬሽን ቢሮ ባለሙያ አቶ ኡስማን ኢድሪስ ሙሳ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡ በአሁኑ ወቅትም አደጋውን ለመከላከል የክልሉ መንግሥት፣ በፌዴራል መንግሥትና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች በጥምረት የፈጠሩት ኮሚቴ እየተንቀሳቀስ ነው ተብሏል፡፡ የተወሰኑ አርብቶ አደሮችም ከብቶቻቸውን የተሻለ አየር ንብረት ወዳለበት አካባቢዎች እየወሰዱ ነው፡፡
የብሔራዊ ሚቲዎሮሎጂ ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር በአፋር አካባቢ ስለተከሰተው ችግር ሲያብራሩ፣ ‹‹በአፋር ክልል ዝናብ ማግኘት በነበረበት ወቅት አላገኘም፡፡ ይህ ትክክል ነው፤›› ብለዋል፡፡
‹‹አሁን ግን በሥርጭትም በሽፋንም የተሻለ ዝናብ በመኖሩ እዚያ አካባቢ ባሉ ግድቦች ውኃ ለመያዝ ያስችላል፡፡ ይህም ከዚህ በኋላ ሊመጣ የሚችለውን ተፅዕኖ መቀነስ የሚያስችል ነው፤›› ሲሉም አክለዋል፡፡
በሌላ በኩል ከዝናብ እጥረት ጋር ተያይዞ በተፈጠረው ችግር ተጎጂ ከሆኑ አካባቢዎች መካከል የአርሲ ዞን ዶዶታ ወረዳ አንዱ መሆኑን የሪፖርተር የመስክ ቅኝት አመላክቷል፡፡ ከሌላው ጊዜ በተለየ የተፈጠረው የዝናብ እጥረት በወረዳው ውስጥ ያሉትን ቀበሌዎች በሙሉ ያዳረሰ መሆኑን የወረዳው ግብርና ቢሮ ገልጿል፡፡ የዝናብ እጥረቱ በግንቦት ወር ከ2,370 ሔክታር በላይ በቆሎ የተዘራበት ማሳ እንዲጠፋ ምክንያት እስከመሆን መድረሱንም፣ የወረዳው የግብርና ቢሮ ኃላፊ አቶ ጀማል ኑራ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
በዝናብ እጥረቱ ምክንያት ለከብቶች መኖ እጥረት በመፈጠሩ አብዛኛዎቹ አርሶ አደሮች ለመጠባበቂያ ያስቀመጡትን መኖ እንዲጠቀሙ አስገድዷቸዋል፡፡ አንዳንዶችም በዚህ ወቅት ለከብቶቻቸው ይሆን የነበረው ሣርና የበቆሎ አገዳ በዝናብ እጥረቱ ምክንያት ባለማግኘታቸው፣ መኖ ወደ መግዛት እንዳስገባቸው ሪፖርተር ያነጋገራቸው አርሶ አደሮች ገልጸዋል፡፡
የዘንድሮው የክረምት ወቅት ዓለም አቀፍ ክስተት የሆነው የኤልኒኖ ተፅዕኖ ሥር በመውደቁ የተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የዝናብ እጥረት ማጋጠሙን የገለጹት ዋና ዳይሬክተሩ፣ እጥረቱም በቦታ በጊዜና በመጠን የተለያየ እንደነበር አስታውሰዋል፡፡ አሁን ግን የተስተካከለ ዝናብ እየተገኘ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
ተመሳሳይና አንድ ዓይነት እጥረት እንዳላጋጠመ፣ በአንፃራዊነት የተሻለ ዝናብ ያገኙ አካባቢዎች እንዳሉ ሁሉ በዚያው ልክ እጥረት ያጋጠማቸው እንዳሉ ለመገንዘብ እንደተቻለ ዳይሬክተሩ ገልጸዋል፡፡ የኤጀንሲው የሚቲዎሮሎጂና የቅድመ ማስጠንቀቂያ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ዶ/ር ድሪባ ቆርቻ፣ በዚህ ወቅት የተፈጠረው ችግር ከኤሊኒኖ ጋር የተያያዘ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ ከዚህ በኋላ በቀጣዮቹ ሁለት ወራት የተሻለ ዝናብ ቢጠበቅም በአሁኑ ጊዜ እየተጠናከረ ከመጣው የኤልኒኖ ክስተት ጋር ተያይዞ በቀሪዎቹ ነሐሴና መስከረም በመደበኛ ሁኔታ የሚኖረው የዝናብ መጠንና ሥርጭት የተዛባና ያልተስተካከለ እንደሚሆንም፣ ኤጀንሲው ባወጣው መግለጫ አመልክቷል፡፡
የዝናብ እጥረቱ ተከስቶባቸዋል ብለው በምሳሌት ከጠቀሷቸው አካባቢዎች መካከል በትግራይ፣ በአማራ፣ በኦሮሚያ፣ በደቡብ፣ በአፋር፣ በሱማሌ አንዳንድ ቦታዎች እጥረቱ በቀጥታ ከኤልኒኖ ጋር በተያያዘ የተፈጠረው ችግር እንደሆነም ታውቋል፡፡ እንደ ኢትዮጵያ ሁሉ ተመሳሳይ የአየር ንብረት ያላቸውና በምድር ወገብ አካባቢ ባሉ አገሮችም የታየ እንደሆነ ተገልጿል፡፡
በአብዛኛው የአገሪቱ ክፍሎች የተከሰተውን የዝናብ እጥረትና ሥጋት የታወቀው ቀደም ብሎ ቢሆንም፣ መረጃው ዘግይቶ መነገሩ አነጋጋሪ ሆኗል፡፡ በተለይ ብሔራዊ ሜቲዎሮሎጂ ኤጀንሲ አሁን የሰጠው መረጃ የዘገየ ነው የሚል ጥያቄ አስነስቶበታል፡፡ የኤጀንሲው ኃላፊዎች ግን መረጃው ዘግይቷል የሚለውን ትችት አልተቀበሉትም፡፡ ኤጀንሲው የክረምቱን ወቅት የተመለከተ ዝርዝር መረጃውን በግንቦት ወር መስጠቱን የገለጹት ዋና ዳይሬክተሩ፣ ከመረጃው በኋላም ላለፉት ሁለት ወራት ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋር ሲሠሩ መቆየታቸውን አስረድተዋል፡፡
ምክትል ዳይሬክተሩ አቶ ዱላ ሻንቆ ኤጀንሲው እያንዳንዱን መረጃ በተለያዩ መንገዶች ሲያቀርብ ስለነበር መረጃውን ለመስጠት መዘግየት ታይቷል የሚለውን ሐሳብ ሳይቀበሉት ቀርተዋል፡፡ ችግሩ መኖሩን በግንቦት ወር ማስታወቃቸውንና የየዕለቱን የአየር ፀባይ መረጃ በመመዝገብና በቀጣይ ሊኖር የሚችለውን ሁሉ በማጠናቀር፣ ከጠቅላይ ሚኒስቴር ጽሕፈት ቤት ጀምሮ ጉዳዩ ለሚመለከታቸው አካላት በሙሉ ማሠራጨቱንም ገልጸዋል፡፡
በዚሁ በመረጃ መሠረት ያለውን ሥጋት እንዴት ለመፍታት እንደሚቻልና መንግሥት ዝግጅት እያደረገ መቆየቱን፣ በብሔራዊ ደረጃ የአደጋ መከላከል ኮሚቴም መቋቋሙ ተገልጿል፡፡ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን የሚመራው ይህ ብሔራዊ የአደጋ መከላከል ኮሚቴ ውስጥ በዋናነት የተካተቱትም ብሔራዊ ሚቲዎሮሎጂ ኤጀንሲ፣ ግብርና ሚኒስቴር፣ የአደጋ መከላከል ዝግጁነትና የምግብ ዋስትና ቢሮ፣ የውኃ፣ መስኖና ኢነርጂ ሚኒስቴር ናቸው፡፡ ይህ ኮሚቴ ሰፊ ርቀት መጓዙን አቶ ፈጠነ ገልጸው፣ ‹‹ጉዳዩ በደንብ ታስቦበት እየተሠራበት ነው፤›› ብለዋል፡፡
ከዚህም በተጨማሪ ከችግሩ አሳሳቢነት አንፃር ኤጀንሲው በየክልሉ ያሉት የቅርንጫፍ የሥራ ኃላፊዎቹ ከየክልሉ ፕሬዚዳንቶች ጋር በቀጥታ በመገናኘት መረጃ እንዲሰጡ ጭምር እየተደረገ ነው ተብሏል፡፡ በይፋ ጋዜጣዊ መግለጫ አልተሰጠበትም እንጂ ሊኖር የሚችለውን ችግር በቅድሚያ በማሳወቅ በጋራ እየተሠራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ሊከሰት ይችላል ተብሎ ከተተነበየው መረጃ አንፃር መንግሥት ሰፊ ዝግጅት እንዲያደርግ ኤጀንሲው መምከሩን፣ የግብርና ዘርፎች በየደረጃው በመዋቅራቸው መሠረት አርሶ አደሮች ዘንድ እንዲደርሱም ከፍተኛ ጥረት መደረጉን ገልጸዋል፡፡
የኤጀንሲው ዋና ተግባር ትንበያና የምክር አገልግሎት መስጠት መሆኑን የገለጹት ዋና ዳይሬክተሩ፣ ቅድመ ማስጠንቀቂያዎችን ጉዳዩ የሚመለከታቸው የውሳኔ ሰጪ አካላት እንዲጠቀሙበት እያደረገ ነው ብለዋል፡፡
አሁን የታየው የአየር ለውጥ የሚያሳርፈው ተፅዕኖ ቀላል ያለመሆኑን ለመግለጽ፣ ‹‹ተፅዕኖው በአንድ አርብቶ አደርና በአርሶ አደር ላይ የሚገለጽ ሳይሆን በጤና ረገድም የራሱ የሆነ ተፅዕኖ ያሳድራል፤›› ብለዋል፡፡
የሚታየው ሙቀት እየተጠናከረ በሚሄድበት ጊዜ በአየር ለውጡ ምክንያት የሚወለዱ በሽታዎችን ጭምር የሚያስፋፋ ከመሆኑ ጋር ተያይዞ፣ ከጤና ዘርፍ ባለድርሻ አካላት ጋር ኤጀንሲው እየሠራ መሆኑንም አብራርተዋል፡፡
የዝናብ እጥረቱም ሆነ የአየር ለውጡ ሌሎች ተፅዕኖዎችን ሊያሳድሩ እንደሚችሉ የኤጀንሲው ኃላፊዎች አስረድተዋል፡፡ የአየር መዛባቱ በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች ላይ ከባድና ቅፅበታዊ ዝናብ፣ ጎርፍና የወንዞች ሙላትን አስከትሏል ተብሏል፡፡
በቀጣይ ወራትም ተመሳሳይ ችግር ሊኖር የሚችልበት ዕድል አንደሚኖር ያመለከቱት ዶ/ር ድሪባ፣ በአንዳንድ አካባቢዎች በአጭር ቅጽበት ከ50 እስከ 80 ሚሊ ሊትር ዝናብ መመዝገቡን አስታውሰዋል፡፡ በቀጣዮቹ ሁለት ወራት በተለይ በነሐሴ ወር የተሻለ ዝናብ ሊኖር ይችላል የሚል ግምት ያላቸው ዶ/ር ድሪባ፣ በበጋ በአንድ በኩል ወቅቱን ያልጠበቀ ዝናብ በደረሱ ሰብሎች ላይ ተፅዕኖ እንደሚኖረው፣ በሌላ በኩል ግን ዝናቡ አዎንታዊ ገጽታ እንደሚኖረውም ያስረዳሉ፡፡ አሁን በተተነበየው መረጃ መሠረት በመጪው በጋ ዝናቡ የሚኖረው ደግሞ የጎርፍና የወንዞች ሙላትን ሊያስከትል እንደሚችልም ተገልጿል፡፡
ከኤልኒኖ ወይም ከሌሎች ክስተቶች ጋር ተያይዞ በአገሪቱ ሊከሰቱ የሚችሉትን ከመደበኛ ወጣ ያሉ የአየር ሁኔታና ፀባይ፣ ክስተቶችንና ተፅዕኖዎችን የዕለት ተዕለት ክትትል በማድረግ መረጃዎችን ለተጠቃሚዎች እንደሚሰጥም ኤጀንሲው አስታውቅል፡፡ አሁን ያለው ችግር ተፅዕኖ ያለው መሆኑ ባይካድም፣ ሰሞኑን የታየው ዝናብ ፍራቻ ያሳደረውን ድርቅ እንዲቀንስ ያደርጋል የሚል ተስፋ እንዳለ ኃላፊዎቹ ጠቁመዋል፡፡
ሰሞኑን የታየው ዝናብ ተስፋ ሰጪ ቢሆንም አሁንም እስከታች ድረስ ሊከናወኑ ይገባቸዋል የተባሉ ጥንቃቄዎችም ተጠቁመዋል፡፡ በተለይ የሚገኘውን ውኃ በተቻለ መጠን መያዝ አስፈላጊ ነው ተብሏል፡፡ ኤጀንሲው ሊፈጠር የሚችለውን ሥጋት ሲገልጽ፣ አርሶ አደሮችና አርብቶ አደሮች ሰብሎቻቸውና እንስሳቶቻቸው እንዳይወድሙና እንዳይሞቱ ለምን አልተደረገም ለሚለው ጥያቄ፣ በኤጀንሲው ኃላፊዎች ምላሽ ሳይሰጥበት ታልፏል፡፡
- See more at: http://satenaw.com/amharic/archives/9515#sthash.qUM8KQzh.dpuf

No comments:

Post a Comment