የተደበቀው የህወሓት ማንነት ከደደቢት እስከ ቤተ መንግስት
ክፍል አምስት
==============================================
"...ሰፊው የትግራይ ህዝብ ስራ አጥቶ በሴተኛ አዳሪነትና ስደት ብቻ ሳይሆን በርሃብ፣ በድንቁርና እና በሽታ እየተሰቃየ በመኖሩ ምክኒያት ጠብመንጃ አንስተን በርሃ ለመውረድ ቻልን..."
ብሎን ነበር ህዝባዊ ወያኔ ሓርነት ትግራይ ያኔ በሽፍትነት ዘመኑ በ1968 ዓ.ም ባሳታመው የፖለቲካ ፕረሮግራሙ ከወደ ደደቢት፡፡
ህዝባዊ ወያኔ ሓርነት ትግራይ ይህን ካለ ከ40 ዓመታት በኋላ ዛሬም ረሃብ፣ በሽታ፣ ስራ አጥነት፣ ሴተኛ አዳሪነት፣ ድንቁርና እና ስደት አለ፡፡ እንዴውም ያን እሱ የተቸውን ዘመን በመሚያስመግን ሁኔታ፡፡ ታግየለታለሁ የሚለውን ትግራይን ጨምሮ መላው የኢትዮጵያ ወጣት በየቀኑ በግፍ ይሰደዳል፡፡
ስደትን አስቆማለሁ ብሎ ጠብመንጃ ያነሳው ህወሓት በስልጣን ዘመኑ ለዕልፍ አዕላፍ ኢትዮጵያዊያን ተሰዶ በባህር በዱር በገደልና በበርሃ ማለቅ ዋነኛ ምክኒያት ሆነ፡፡
ድህነትን ከአገራችን ምድር አጠፋለሁ ብሎ ታጥቆ የተነሳው ህወሓት ኢትዮጵያን ከኒጀር ቀጥላ የዓለም ሁለተኛዋ መናጢ ደሃ አገር ሆና በውርደት መዝገብ ስሟ እዲሰፍር አድርጎ ገናና ታሪኳን ሙልጭ አድርጎ ከምድረ ገፅ አጠፋው፡፡
ኮሌጅ የበጠሱ ወጣቶች የህወሓት ትምህርት ሜኒስቴር የሰጣቸው ክርታስ እንጀራ ሊያስቆርሳቸው ባለመቻሉ ረጅም የስደት ጅረት በመፍጠር ልክ እንደወንዞቻችን የተፈጥሮ ሀብታችንን ተሸክመው ያለማቋረጥ ወደ ውጭ መፍሰሳቸውን ቀጥለዋል፡፡ የመን ውስጥ ብቻ 800 ሺህ ወጣቶች እንደሚገኙ ዓለም አቀፍ የፍልሰት ድርጅት /I.O.M/ ያወጣው ሪፖርት ያረጋግጣል፡፡