Sunday, October 22, 2017

በሕወሐት፣ኦህዴድና ኦነግ በተቀነባበረ ሴራ በንፁሐን ዜጎች ላይ የሚደርሰው ተደጋጋሚ ጭፍጨፋ ታሪክ ይቅር የማይለው አረመኒያዊ ተግባር ነው!!! (ከሰማያዊ ብሔራዊ ሸንጎ የተሰጠ መግለጫ)


አገዛዙ እያረጀና የመውደቂያ ዘመኑ መቃረቡን ተከትሎ የአገዛዙን ግብዓተ መሬት ለማፋጠን በሐገራችን በተለያዩ አካባቢዎች የተቀሰቀሱ አመፆች ቀጥለው አሁን በአንዳንድ አካባቢዎች ሕዝባዊ እንቅስቃሴዎቹ መልካቸውን እየቀየሩ ከአገዛዙ ጋር ግንኙነት የሌላቸውን ዜጎችን በአሰቃቂ ሁኔታ ወደ መግደልና ማሳደድ ተቀይረዋል፡፡ በተለያዩ የመገናኛ ብዙሃን እንደተገለፀው የተነሳውን ሕዝባዊ እንቅስቃሴ ተክትሎ በኦሮምያ ክልል ቡኖ በደሌ ዞን ጮራና ዴጋ ወረዳዎች በሚኖሩ አማሮች ላይ በተሰነዘረ ጥቃት ብዙ ዜጎች በገጀራ አንገታቸው እየተቀላ በአሰቃቂ ሁኔታ እንደተገደሉ፣ቤት ንብረታቸው እንደተቃጠለና ከጥቃቱ የተረፉትም ህይወታቸውን ለማዳን በቤተ ክርስቲያን እንደተጠለሉና ገሚሶቹም በጫካ ውስጥ ተጠልለው እንደሚገኙ ታውቋል፡፡ 
ሕወሐት/ኢሕአዴግ በተከለው የዘረኝነትና የጥላቻ ፖለቲካ በተለያየ ጊዜ በተለያዩ የሐገራችን አካባቢዎች የኢትዮጵያውያን ሞት፣የንብረት መውደምና ከቀዬቸው መፈናቀል በየጊዜው የምንሰማው መርዶ ነው፡፡ ይህ የአገዛዙ የጥላቻ መርዝ ቀስቱ ከመነሻው ጀምሮ በአማራ ላይ ያነጣጠረ መሆኑን እራሱ አገዛዙ በአዘጋጃቸው ሰነዶች ላይ በግልፅ ተቀምጧል፡፡ አገዛዙ ይህንን በዚህ ህዝብ ላይ የጥፋት ተልዕኮውን ለማስፈፀም በሕወሐት የሚዘወር ኢሕአዴግ የሚባል ሽፋን እየተጠቀመ ተደጋጋሚ የሆነ የግድያና የማፈናቀል ተግባሩን ተያይዞታል፡፡
ብአዴን የሚባለው የሕወሐት ጉዳይ አስፈፃሚ ድርጅት አውክለዋለሁ የሚለውን ህዝብ ከመፈረጅና ከማጥላላት አልፎ የአማራ ህዝብ ለሚደርስበት ግድያ፣መፈናቀልና የንብረት ውድመት ምንም ዓይነት ተግባራዊ እርምጃ ያልወሰደና በዝምታ የሕወሐት የጥፋት ተልዕኮ ተባባሪ በመሆን የአገልጋይነት ተግባሩን ቀጥሎበታል፡፡
ኦህዴድና ኦነግም የአማራን ህዝብ ለኦሮሞ ህዝብ ጠላት አድርጎ ፕሮፓጋንዳ በመንዛትና የጥላቻ ሀውልት በማቆም የአማራን ህዝብ በየጊዜው ለግድያ፣ለንብረት ውድመትና መፈናቀል እንዲዳረግ አድርገውታል፡፡
አንዳንድ ወገኖች በተለያዩ ጊዚያት በአማራ ህዝብ ላይ የሚደርሰውን ጭፍጨፋ በአማራና ኦሮሞ ህዝብ ተራ ዜጎች መካከል የተፈጠረ በሁለቱም በኩል ያለ ጥላቻ አድርገው ለመሳል ይሞክራሉ፡፡ ነገር ግን ይህ አመለካከት ከእውነት የራቀና መሬት ላይ ያለውን ሀቅ የማይወክል መሆኑን ለማረጋገጥ በኦሮሚያ ክልል መንግስት የተሰራውን የጥላቻ ሀውልት እና የአማራ ህዝብ በተደጋጋሚ ጊዜ ግድያና መፈናቀል የሚደርስበት በኦሮሚያ ክልል ሲሆን በአማራ ክልል ውስጥ የሚኖሩ የኦሮሞ ህዝብ ግን የግድያም ሆነ የማፈናቀል ተግባራት ተፈፅሞባቸው አያውቅም፡፡ ስለሆነም በአማራ ህዝብ ላይ እየተፈፀመ ያለው ፍጅት በንቃት በድርጅት በተለይም በሕወሐት፣በኦህዴድና በኦነግ የተቀነባበረ ፀረ አማራ ተግባር ነው፡፡ በመሆኑም ሀገር አስተዳድራለሁ በማለት ኃላፊነት የወሰደው ሕወሐት/ኢሕአዴግ እስካሁኗ ሰዓት ድረስ በአማራ ህዝብ ላይ ለደረሰው ጥፋት በህግም ሆነ በታሪክ ከተጠያቂነት አያመልጥም፡፡ የቅርብ ጊዜ ታሪካችንን ብንመለከት በጨቋኙ የደርግ አገዛዝ ዘመን ዜጎች እርስ በእርስ በጥላቻና በመናናቅ ተነሳስተው የተፈፀመ የጎላ ግጭት አልነበረም፡፡ እንዲህ አይነት አረመኒያዊ ተግባር ተጠንስሶና ተሰርቶበት ያደገው በሕወሐት/ኢሕአዴግ የአገዛዝ ዘመን ነው፡፡
በመሆኑም ይህንን ችገር ከመሰረቱ ለመንቀል የኢትዮጵያ ህዝብ ሕወሐት፣ኦህዴድና ኦነግ በሚረጩት የጥላቻ መርዝ ሳይፈታ የቀደመ ጨዋነት፣ሆደሰፊነትና መከባበር እሴቶችን በመጠበቅ ከሚደርስበት የመጠፋፋት ተግባር እራሱን እንዲከላከል እያሳሰብን የችግሮች ሁሉ ምንጭ የሆነውን ሕወሐት/ኢሕአዴግን ለማሶገድና ህዝባዊ አስተዳደር ለመትከል የጀመረውን ትግል አጠናክሮ እንዲቀጥል ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡
ጥቅምት 12 ቀን 2010 ዓ.ም
አዲስ አባባ

No comments:

Post a Comment