Friday, June 12, 2015

ግልጽ ደብዳቤ ለጥላሁን ገሰሰ ቤተሰቦች

June 10, 2015
ንዋይ ደመረ
ከሁሉም በማስቀደም የከበረ ሰላምታዬ በያላችሁበት ይድረሳችሁ። በዋነኛነት ይህንን ደብዳቤ ልጽፍ ያነሳሳኝ ሰሞኑን በአንድ በጥላሁን ገሰሰ ስም የሚነግድ “መስፍን” በዙ የተባለ ተራና ስብእና የጎደለው አጭበርባሪ ግልሰብ ታማኝ በየነ ለምን ክብርና ሽልማት አገኘ በሚል በአደባባይ “ታማኝ በየነ ገዳይ እና ከፋፋይ” ነው ከማለት አልፎ ግለሰቡ በጥላሁን ገሰሰ ስም (Tilahun Gesesse TV / TGTV) በሚለቀው እውር ድንብሩ በወጣ ቪዲዮ ወያኔን አወድሶ ለአገራቸው መልካም የሚሰሩ ኢትዮጵያዊያንን ስም ለማጠልሸት ጥረት ሲያደርግ በተደጋጋሚ በማየቴ ነው።
Mesfin Bezu wanna be Tilahun Gessese
እንደሚታወቀው ታላቁ የሙዚቃ ንጉስ ጥላሁን ገሰሰ በኢትዮጵያ ህዝብ ታሪክ ውስጥ ልዩ ስፍራ ይዞ የሚ
ገኘው ጊዜ በማይሽራቸው የጥበብ ስራዎቹ ብቻ ሳይሆን ለአገሩና ለህዝቡ በነበረው ጥልቅና ልባዊ ፍቅር እንደ ነበር ጭምር ማንም የሚያውቀው ሃቅ ነው። ጥላሁን ከፍቅር ባሻገር፣ በርካታ ግዙፍ መልእክት ያላቸው ዘፈኖችን እንዲሁም ልብ ውስጥ በልዩ ተሰጥኦው ጣእም ባላቸው ዜማዎቹ ዘልቆ በመግባት የአገርና የህዝብ ፍቅርን እና አንድነትን አስርጿል ብል ፈጽሞ ማጋነን እንደማይሆንብኝ ከትውልድ ትውልድ የሚተላለፉ ስራዎቹ ይመሰክራሉ። ስለዚህም ነው እኔም እንደ አንድ ኢትዮጵያዊ ዜጋ የጥላሁንም ይሁን የቤተሰቡ ስም ያለ አግባቡ በተራ ሁኔታ በየመንገዱ ሲነሳ እና ጭቃ ሲቀባ ማየት የሚከነክነኝ።
ምንም እንኳን ጥላሁን በአካል ቢያልፍም ከኢትዮጵያ ህዝብ ፍቅርና ክብርን የተጎናጸፈባቸው በርካታ ስራዎቹን ትቶልን ስላለፈ የዚህን ታላቅ ኢትዮጵያዊ መልካም ስም፣ ታሪክና ቅርስ መጠበቅ የሁላችንም ድርሻ ቢሆንም በተለይ እናንተ የቅርብ ቤተሰቦቹ ከፍተኛ ሃላፊነት እንዳለባችሁ እውን ነው። ይህንን ደብዳቤ ልጽፍላችሁም ያነሳሳኝን ጉዳይ ሳቀርብ እናንተም ሆናችሁ የጥላሁን ገሰሰ ክብርና ስም ያለአግባቡ እንዳይነሳ ለጉዳዩ ትኩረት ሰጥታችሁ መፍትሄ እንደምታፈላልጉለት በመተማመን ነው።
የጥላሁን ገሰሰ ባለቤት የነበሩት የወ/ሮ ሮማን በዙ ወንድም እንደሆነ በየአጋጣሚው የሚያውጀው “መስፍን በዙ”የተባለው ይህ ግለሰብ ይህን ታላቅ ኢትዮጵያዊ በተለያዩ መንገዶች ለማስታወስና ለመዘከር ሲነሳ ከጥላሁን ክብር፣ ዝናና ደረጃ ጋር ተመጣጣኝ የሆነ ስራ ማቅረብ እንደሚጠበቅበት የአደባባይ ሚስጢር ነው። ይሁንና ባለፍት ጥቂት አመታት “መስፍን በዙ” Tilahun Gessese TV / TGTV በሚል ስም እራሱ ደንቁሮ ሌሎችን ለማደናቆር መጣጣሩ ብቻ ሳይሆ የጥላሁንን ገሰሰን ስም በየአደባባዩ ማቆሸሹ አስተዛዛቢ ሆኗል።
ይሄው ግለሰብ ጥላሁን ገሰሰን በቪዲዮ ስርጭት ለመዘከር መንቀሳቀሱ መልካም ቢሆንም ከጥላሁን ስብእና፣ እምነት፣ ስምና ክብር ጋር ሙሉ በሙሉ በሚጻረር መልኩ በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ አስከፊ ግፍ፣ ወንጀልና ዘረፋ ከሚፈጽሙት አንባገነኖች ለሚወረወርለት ዳረጎት ህሊናውን ሽጦ አሳፋሪ ስራ በጥላሁን ገሰሰ ስም በመስራት ላይ መሆኑን ለማወቅ ግዜ የሚፈጅ ጉዳይ አይደለም። በእርግጥ ግለሰቡ እንኳን በሌላው ኢትዮጵያዊ ወያኔዎቹም የሚቀልዱበትና የሚሳለቁበት ስለሆነ በህይወቱ ክብደት ያለው ቁምነገር ተናግሮ ፋይዳ ያለው ለውጥ ያመጣል ብሎ ማንም እደማይጠብቅ ግልጽ ነው። ከሁሉም በላይ ደግሞ ግለሰቡ የሚታወቀው በኪሳራ (bankruptcy) ህይወቱን መምራት የተሳነው በተቀጠረበትም ይሁን በተገኘበት ሁሉ እንደክፉ ውሻ የሚባረር የተጠላና ተራ ሰው በመሆኑ ለእርሱ በቀጥታ መልስ መስጠት እራስን ማዋረድ ነው የሚል እምነት አለኝ።
“ውሸት ለመናገር አትሻም ምላሴ” እያለ ጥላሁንን እያዘፈነ በውሸት እና በማደናገር ላይ ያተኮረ አሳፋሪና ከንቱ ስራ እንዴት ጥላሁንን ሊዘክር እንደሚችል ትልቅ እንቆቅልሽ ነው። ሆድ ለመሙላት ሲባል በህዝባችን ላይ ተዘርዝሮ የማያልቅ ወንጀል ዘውትር የሚፈጽሙ አንባገነኖችን አወድሶ የሚኖር ሰው ስለ እውነት በአደባባይ ቆሞ ሲዘፍን እና ሲያዘፍን ማየት አስቂኝም አሳዛኝም ጉዳይ ነው።
ለእውነት የቆመ ማንም ሰው ጥላሁን ከአጼ ሃይለስላሴ ዘመን ጀምሮ እስከ ህልፈተ ህይወቱ የአገሩን ህዝብ ጉስቁልና፣ እረሃብ፣ ፍትህ መነፈግና የነጻነት እጦት በሚችለው አጋጣሚ ሁሉ አጉልቶ ለማሳየት ሲያደርግ የነበረውን ጥረት ሊዘነጋ አይችልም። ለእውነት የቆመ ሰው ከሆዱ ይልቅ ለህሊናው ይገዛል። ለእውነት የቆመ ሰው የህዝቡ ህመም ይሰማዋል፣ ግፍ፣ ሰቆቃው፣ ግድያ፣ ስደትና ጉስቁልናው ሁሉ ያመዋል። ለእውነት የቆመ ሰው ወገኖቹ በሃሰት እየተወነጀሉ በየአደባባዩ ሲገደሉ በየእስር ቤቱ ከቤተሰቦቻቸው እና ልጆቻቸው ተለይተው ሲሰቃዩ አላየሁም አልሰማሁም ብሎ ዘወትር ይህን ሁሉ ወንጀል የሚፈጽሙ ዘረኞችና ፋሺስቶችን ሲያወድስ የሃሰት እድገት፣ ፍትህና ሰላም ሲዘክር ግዜውን አያጠፋም። ለእውነት የቆመ ሰው ህሊናውን እንደሸቀጥ ለሳንቲምና ለፍርፋሪ አደባባይ አውጥቶ አይቸረችርም። ለእውነት የቆመ ሰው አላዋቂነቱን እንደ እውቀት ይዞ አደባባይ እየወጣ አስምስሎ አይኖርም። ታዲያ ይሄ ግለሰብ የሚሰራው እርካሽ ስራ እየታወቀ ጥላሁን ገሰሰን አክብሮ ሊያስከብረው የተነሳው ምን ቁም ነገር ይዞ ነው? መልሱን ለእናንተ እተወዋለሁ።
ለታማኝ በየነ መከበርና መሸለም አዲስ ነገር አይደለም። ታማኝ ለምን በወገኖቹ ዘንድ እንደሚከበር የታወቀ ጉዳይ ስለሆነ ድምጽ አልባ ለሆነ ህዝብ ድምጽ የሆነ ሰው በመሆኑ ለእውነት፣ ለፍትህ፣ ለመብትና ለነጻነት ለሚደረገው መራራ ትግል ያበረከተውን አስተዋጽኦ መዘርዘር ለቀባሪው አረዱት ስለሆነ መዘርዘር አያስፈልገኝም። ይሁንና እርካሹና በውሸትና በማጭበርበር የገለማው ግለሰብ መሰሎቼን አስተባብሬ “ታማኝን የተቃወምኩት ገዳይና ከፋፋይ በመሆኑ ብቻ ሳይሆን በጥላሁን ገሰሰ ላይ ከፍተኛ ክህደት በመፈጸሙ ነው” ብሏል። ይህ እርካሽ ክስ ማንን እንመን አያስብልም። መስፍን በዙ የህይወት አቅጣጫ የጠፋበት፣ ከቻይና ሳይቀር በህገወጥ ድርጊቱ የተባረረ መልካም ስብእናና ጤንነት የጎደለው ለእውነት ሳይሆን ለርካሽ ፍርፋሪ የሚሯሯጥ አጭበርብሮ እና ውሸትን ቸርችሮ ከርሱን የሚሞላ ግለሰብ ስለሆነ የእርሱን ከንቱ ክስ ወደ ጎን ተወት አድርገን የተከበረችው የጥላሁን ገሰሰ ልጅ ወ/ሮ ንፁህ ብር ጥላሁን ስለ ታማኝ በየነ በአደባባይ የተናገረችውን ወደሁዋላ መለስ ብለን እናስታውስ።
የዛሬ አራት አመት በዋሺንግተን ዲሲ ለታማኝ ልዩ የክብር ስነስርአት ተዘጋጅቶ ነበር። በዛ የክብር ስነስርአት የሰውን ሁሉ ቀልብ የሳበ ንግግር ከማረግ በላይ አባቷ ከአገሯ ስትወጣ የሰጣትን ቀለበት ለማስታወሻነት ጥላሁን እንደ ልጁ ለሚያየው ለታማኝ በእንባ ታጅባ ማስረከቧ በቪዲዮ ተቀርጾ በአለም ዙሪያ የታየ ሃቅ ነው። ወ/ሮ ንፁህ ብር ጥላሁን ልጄ ነው የሚለውን ታምኝ ያደረገውን ውለታ በጥቂቱ ከዘረዘረች በሁዋላ እንዲ ነበር ያለቸው፣
“ሌላ የማደርገው ነገር የለም። ግን በአባትነቱ ከአገር ስወጣ ጥላሁንዬ ኤርፖርት ላይ መጨረሻ ጠርቶ ከእጁ አውልቆ የጣቱን ወርቅ ሰጥቶኛል። ይሄን የሰጠኝን ስጦታ እኔ ደግሞ ታማኝን እጅግ አድርጌ ስለምወደው ታማኝ ጥላሁንዬ ባይወልደውም የእርሱ ልጅ መሆኑን አረጋግጦለት የሄደውን ይሄን ስጦታ ለእርሱ አሳልፌ እሰጣለሁ።”
ይሁንና መስፍን በዙ የተባለው ይሄ ርካሽ ግለሰብ የቅናት መሆኑ ግልጽ በሆነ መልኩ ሶስት በርካሽ እና ተራ ክስ የተሞላ ቪዲዮ ሰርቶ በማሰራጨት የታማኝን ስም ለማጥፋት ሙከራ አድርጓል። የሚያሳዝነው ደግሞ ይሄንኑ የቪዲዮ ቆሻሻ የዛሬ ሶስት አመት ገደማ የለቀቀው በጥላሁን ገሰሰ ስም (Tilahun Gesesse TV / TG TV) ብሎ በሰየመው የወያኔ መጠቀሚያ የቪድዮ ቆሻሻ አሸንዳ መሆኑ ነው። ከዚህም በተጨማሪ ለኮሚዩኒቲ አገልግሎት በነጻ ለማህበረሰብ ጥቅም እንዲውል በተቋቋመው የሜሪላንድ ሞጎሜሪ ኮሚዩኒቲ ሜድያ በኩልም አሰራጭቷል። በእርግጥ የኮምዩንቲው ድክመት እንጂ በኢትዮጵያውያን ስም እንዲህ አይነት የረከሰና ተራ ፕሮፓጋንዳ ሊሰርሰራጭ አይገባም ነበር።
ሌላው ከሰሞኑ ያሰራጨው ቪዲዮ የቀድሞው አንባገነን መለስ ዘናዊን እንደጣኦት ያመልኩ የነበሩ የህወሃት ጀሌዎችና አጋፋሪዎቻቸው በአለም መሪዎች ፊት ጣኦታችንን አዋረድክ በሚል ስሜት በጋዜጠኛ አበበ ገላው ላይ በተቀነባበረ መልኩ ከፍተኛ የሆነ ዛቻ፣ የስም ማጥፋት እና አደገኛ ቅስቀሳ ላይ ተጠምደው እንደነበር የማይዘነጋ ነው። ከዚህ ጋር በተያያዘ ቢያንስ የተወሰነኑትን በህግ ተጠያቂ ለማድረግ እንቅስቃሴ ለማድረግና የራሱንም ሆነ የቤተሰቡን ደህንነት ለማስጠበቅ ብዙም ባይሆን ገንዘብ መሰባሰቡ መስፍን በዙ እንዳለው አዲስ ግኝት ሳይሆን በይፋ የተከናወነ የአደባባይ ሚስጥር ነው።
በዚህ በሰለጠነው አለም ማንም ሰው ህጋዊ እርምጃ ሲወስድ በሚስጥር ሳይሆን በአደባባይ ነው። እኔ በቀላሉ ማረጋገጥ የቻልኩት ሀቅ አበበ ገላው የህገ ወጡ ቅስቀሳ መሪ ተዋናይ የሆኑትን የአይጋውን ኢሳይስ አባይና ነዋሪነቱ በአትላንታ የሆነ ተባባሪው ላይ በካሊፎርንያ ሳንታ ክላራ እና በአትላንታ ደክላብ ካውንቲ ፍርድ ቤቶች ክስ መስርቶ ‘ንደነበር ማንም በቀላሉ ሊያጣራው የሚችለው ሃቅ ነው። በተጨማሪም ተቀመጭነቱ አትላንታ የሆነው ጠበቃ ዲክሰን ጄምስ [Georgia Bar No. 003989] አበበን የወከለው ሌላውን ወጪ ሳይጨምር በሰአት 250 ዶላር (ያውም በቅናሽ) እየተከፈለው እንደነበር ጠይቆ መረዳት ይቻል ነበር። መስፍን በዙ አላማው ስም ማጥፋት ስለሆነ ብቻ ፈጽሞ በማይመለከተው ጉዳይ የማያውቀውን ዲስኩር ሲያሰማ ታዝበናል።
በአሁኑ ግዜ ክሱም የተቅዋረጠው እንደውም በቂ ገንዘብ ባለመሰባሰቡ እንደሆነ እኔ በበኩሌ የማውቀው ሃቅ ነው። አላዋቂ ሳሚ እንዲሉ አንባገነኑ መለስ አልደነገጠም ታንክ ተደግፎ መጻሃፍ ያነብ ነበር FBI የግድያ ሴራ አላከሸፍኩም አለ ምናም በማለት ለዘባረቀው ከሃቅ የራቀ ዲስኩር እውነቱ ስለሚናገር ማንም መልስ ሊሰጠው አይገባም ብዬ አምናለሁ። ይሁንና በሃሰት የተከሰሰ ግለሰብ ካለ ታዲያ ለምን ወደ ፍርድ ቤት ጎራ ብሎ ባልፈጸምኩት ወንጀል ስሜ ጠፋ ብሎ አይከስም፣ FBIስ ቢሆን ብስሙ ሐሰት ሲሰራጭ እንዴት ዝም አለ። ይሁንና መስፍን በዙ በጥላሁን ገሰሰ ስም እነዚህ ጉዳዮች ውስጥ ምን ያገባዋል። በጥላሁን ስም ከመዘባረቅ ለምን በራሱ ስም አይዘባርቅም። መሰረታዊውን እውነታም ቢሆን የጉዳዩ ባለቤት የሆነው ጉሽ አበራም በአደባባይ ለመካድ አልደፈረም።
እነዚህን ጉዳዮች ከብዙው በጥቂቱ ያነሳሁት ግለሰቡ በሁሉም ኢትዮጵያዊ ዘንድ በተከበረውና በታላቁ የሙዚቃ ንጉስ በጥላሁን ገሰሰ ስም ተራ እና እርካሽ ፕሮፓጋንዳ እንዳይሰራጭ እንድታደርጉ በትህትና ለመጠየቅ እወዳለሁ። ይሄንን መስፍን በዙ የተባለ ማፈሪያ ግለሰብም ቢያንስ እህቱ ወ/ሮ ሮማን በዙ ለርሳቸውና ለመላው ቤተሰቡ በጥላሁን ገሰሰ ስም መነገድ እና እርካሽ እና አስተዛዛቢ ስራ ከመስራት እንዲቆጠብ እንደሚያደርጉ እተማመናለሁ። ሁሉም በራሱ ስም ይነግድ።
ቸር ይግጠመን!

No comments:

Post a Comment