Thursday, November 23, 2017

በኮማንደር ደሳለኝ ላይ ለተፈጸመው ግድያ አርበኞች ግንቦት7 ሃላፊነቱን ወሰደ (ኢሳት ዜና፣ ህዳር 14 ቀን 2010 ዓም )

በባህርዳር ከተማ የፌደራል ፖሊስ አዛዥ በሆነው ኮማንደር ደሳለኝ ልጃለም ላይ ህዳር 12 ቀን 2010 ዓ/ም ከምሽቱ 4:45 በመኖሪያ ቤቱ ግቢ ውስጥ ለተፈጸመው ግድያ ንቅናቄው ሃላፊነቱን ወስዷል። ግንባሩ ባወጣው መግለጫ የፖሊስ አዛዡ በከተማው ተካሂዶ በነበረው ህዝባዊ ተቃውሞ ላይ ከህወሀት የተሰጠውን መመሪያ በማስፈጸም ለበርካቶች ግድያና ስቃይ ተጠያቂ ነበር።
የኮማንደሩ አስከሬን ከፈለገ ህይወት ሆስፒታል ምርመራ ቢደረግለትም እጅግ ጥበብ በተሞላበት ድምፅ በሌለው መሳሪያ ጭንቅላቱ ላይ ሁለት ቦታ ተወግቶ ሊሞት ችሏል ። ኮማንደሩ በ ብአዴን 37ኛ ዓመት የምስረታ በዓል ላይ ከልዩ እንግዶች ጋር የራት ግብዣ ላይ ተገኝቶ ካመሸ በሁዋላ የስንብት እርምጃ እንደተወሰደበት ግንባሩ ገልጿል።
ግንባሩ አክሎም፣ የመከላከያ የደህንነት የከተማ ምድብ ኃላፊ ሆኖ ሲሰራ የነበረ፣ የህወሓት የደህንነት አባል ህዳር 12 ቀን 2010 ዓ/ም ከምሽቱ 4:15 ሲሆን በባህርዳር ከተማ ቀበሌ 04 ከአንድ ጭፈራ ቤት ሲዝናና በነበረበት ሰዓት በአርበኞች አባላት ታፍኖ ከተወሰደ በኃላ በባህርዳርና በመሸንቲ ከተማ መሃል የግድያ እርምጃ እንደተወሰደበት አስታውቋል። ይህ የህወሓት ወታደራዊ መረጃ መኖሪያውን ባህርዳር አየር ኃይል ምድብተኛ ግቢ በማደረግ ለአለፉት 3 ዓመታት በባህርዳር ከተማ የመረጃ ኃላፊ ሁኖ በርካቶችን ያስገደለ እና በተለይ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የጄኔራል ፍሳሀ እና የጄኔራል ተስፋዬ ዋና አማካሪ በመሆን በርካታ ግፎችን መፈጸሙንም ጠቅሷል። ግንባሩ ተመሳሳይ እርምጃዎችን መውሰድ እንደሚቀጥልም አስታውቋል።
ግንባሩ ባወጣው መግለጫ ዙሪያ የክልሉን ፖሊስ ለማናገር ያደረግነው ጥረት አልተሳካም።

No comments:

Post a Comment