Saturday, November 25, 2017

በመከላከያና በደህንነቱ ዋና መስሪያ ቤት መካከል ያለው አለመግባባት ከፍተኛ ደረጃ ላይ መድረሱ ተሰማ (የአርበኞች ግንቦት 7 ድምፅ ሬዲዮ)


በአቶ ጌታቸው አሰፋ የሚመራው የብሄራዊ መረጃና ደህንነት መስሪያቤት እና በጄነራል ሳሞራ የሚመራው መከላከያ መካከል የተፈጠረው ያለመግባባት በግልጽ የሚታይበት ደረጃ ላይ መድረሱ ታውቋል። በመከላከያ ውስጥ ያሉ ከፍተኛ የጦር አዛዦች የደህንነቱ መስሪያ ቤት የሚያቀርበው መረጃ፤ ታእማኒነት የሌለው ነው በማለት በተደጋጋሚ ሲገልጹ ይሰማል። አቶ ጌታቸው አሰፋ በመከላከያ ውስጥ ያለውን ተሰሚነት ለማስፋት በሚል የሚወስዳቸው እርማጃዎች ቀጥታ ከጄነራል ሳሞራ ጋር እንዳጋጨው መረጃዎች ያመለክታሉ። Image may contain: 2 peopleጄነራል ሳሞራና የእሱ ደጋፊ የሆኑ የጦር አዛዦችን ለመቆጣጠር በሚል አቶ ጌታቸው አሰፋ በመከላከያ ውስጥ ለሱ የሚታዘዝ መረቦችን ለመዘርጋት ያደረገውን ሙከራ ተከትሎ በሁለቱ የህወሃት ቁንጮዎች መካከል ከፍተኛ የሆነ ያለመግባባት ተፈጥሯል። በመከላከያ ውስጥ ለአቶ ጌታቸው አሰፋ ጥሩ ምልከታ አላቸው የሚባሉ ከፍተኛ የጦር አዛዦች ላይ በመከላከያ የወታደራዊ መረጃ ዋና መምሪያ ስር የሚገኘው በመከላከያ ጸረ መረጃ መምሪያ አማካኝነት ከፍተኛ ክትትል እየተደረገባቸው ይገኛል። በአቶ ጌታቸው አሰፋ እና በጄነራል ሳሞራ መካከል ያለውን አለመግባባት ለመቅረፍ በሚል ዶ/ር ደብረጺዮን ገብረሚካኤል እና ሌ/ጄነራል ዮሃንስ ገ/መስቀል ለማሸማገል ያደረጉት ሙከራ አለመሳካቱን ከመከላከያ የተገኘው መረጃ ያመለክታል። ሌ/ጄነራል ዮሃንስ ገ/መስቀል አቶ ጌታቸው አሰፋ ከሚመራው የደህንነቱ ዋና መስሪያቤት ጋር ጥብቅ ቁርኝት እንዳለው ይታወቃል። ሌ/ጄነራል ዮሃንስ ገ/መስቀል አሁን በመከላከያ የወታደራዊ መረጃ ዋና መምሪያ ሃላፊ ከሆኑት ሜ/ጄነራል ገብሬ ዲላ በፊት በመከላከያ የወታደራዊ መረጃ ዋና መምሪያ ሃላፊ እንደነበሩ ይታወሳል። ሌ/ጄነራል ዮሃንስ ገ/መስቀል ከጄነራል ሳሞራ ጋር ባላቸው አለመግባባት ምክንያት ነው ከዚህ ሃላፊነታቸው እንዲነሱ የተደረገው። ሌ/ጄነራል ዮሃንስ፤ አቶ ጌታቸው አሰፋና ጄነራል ሳሞራን ለማስታረቅ ያደረጉት ሙከራም የከሸፈው መጀመሪያውኑ ሌ/ጄነራል ዮሃንስ ገ/መስቀል እና ጄነራል ሳሞራ የሚግባቡ ባለመሆኑ ነው። አቶ ጌታቸው አሰፋ በመከላከያ ውስጥ የሚኖረውን ተጽኖ ለማስፋት ከሚጠቀምባቸው ሰዎች አንዱ ሌ/ጄነራል ዮሃንስ ገ/መስቀል እንደሆነ ይነገራል። ጄነራል ሳሞራ ሌ/ጄነራል ዮሃንስ ከደህንነቱ ዋና መስሪያቤት ጋር ያላቸውን ቅርርብ ጠንቅቆ እንደሚያውቀው ጉዳዩን በቅርብ የሚከታተሉ አካላት ይገልጻሉ። ከዚሁ ጋር ተያይዞ አቶ ጌታቸው አሰፋ በመከላከያ ውስጥ ያለውን ተሰሚነት ለማስፋት በሚል ከዶ/ር ደብረጺዮን ገ/ሚካኤል ጋር በቅርበት እንደሚሰራ ከደህንነቱ መስሪያ ቤት የተገኘ መረጃ ያመለክታል። አቶ ደብረጺዮን መከላከያው ውስጥ ባለው በጎ ግንኙኑነት የተነሳ፤ አቶ ጌታቸው አሰፋ በዶ/ር ደብረጺዮን በኩል ነው፤ በመከላከያ ውስጥ ያለውን ፍላጎት ለማስጠበቅ የሚንቀሳቀሰው ሲሉ በደህንነት ውስጥ ያሉ አካላት ይገልጻሉ። ዶ/ር ደብረጺዮን በመከላከያ ውስጥ ያለውን ተሰሚነት ምክንያት በማድረግ አቶ ጌታቸው አሰፋን እና ጄነራል ሳሞራን ለማግባባት ያደረገው ሙከራ አለመሳካቱ ታውቋል። ጄነራል ሳሞራ አቶ ጌታቸው አሰፋ መከላከያን ለመቆጣጠር የሚያደርገውን ሙከራ እንዲያቆም በሃይለ ቃል መናገሩ ጉዳዩን በቅርበት የሚከታተሉ አካላት ይገልጻሉ። በተጨማሪም የደህንነቱ ዋና መስሪያ ቤት የሚያቀርበው ሪፖርቶች በአብዛኛው በውሸት የተሞሉ በመሆናቸው ከደህንነቱ መስሪያ ቤት የሚመጣን ማንኛውም ሪፖርት በጥንቃቄ እንዲታይ ጄነራል ሳሞራ ትእዛዝ ማስተላለፉን ተከትሎ አቶ ጌታቸው አሰፋን ያስቆጣ ጉዳይ ሆኗል። በአሁን ሰአት ከፍተኛ የጦር አዛዦች ከደህንነቱ ዋና መስሪያ ቤት የሚመጣን ማንኛውንም የመረጃ ሪፖርት ከመጠቀም ይልቅ በመከላከያ ስር ባለው የወታደራዊ መረጃ ዋና መምሪያ በኩል የሚመጡ መረጃዎች ላይ እምነት እንዲያሳድሩ ሆኗል። በመከላከያ የወታደራዊ መረጃ ዋና መምሪያ፤ የደህንነቱ ዋና መስሪያ ቤት የስራ ክልል በሆነው በሲቪል መረጃ ስራዎች ውስጥ መግባቱ በሁለቱ ተቋማት መካከል ለተፈጠረው ያለመግባባት አንዱ ምክንያት እንደሆነ ይነገራል። በመከላከያና በደህንነቱ ዋና መስሪያ ቤት መካከል ያለውን ያለመግባባት ለመፍታት በሚል ተደጋጋሚ ጥረቶች ቢደረጉም እስካሁን ድረስ በጄነራል ሳሞራና በአቶ ጌታቸው አሰፋ መካከል ያለው ግንኙነት እንደሻከረ ይገኛል።

No comments:

Post a Comment