Sunday, January 11, 2015

"አገር ተቃጠለ"

"አገር ተቃጠለ"
በአዲስ አበባ(ኢትዮጵያ) የመጀመሪያው ሆቴል አሁን ፒያሣ የሚገኘው ጣይቱ ሆቴል ነው::
ሆቴሉ በ1898ዓ/ም በነሀሴ ወር ሥራውን ጀመረ:: ሆቴሉን የማስተዳደር ሥራ እቴጌ ጣይቱ ተረክበው ሐላፊነቱን መወጣት ጀመሩ::
በ1900ዓ/ም ጥቅምት25 ቀን ምኒልክ በአዲስ አበባ ያሉ ዲፕሎማቶችንና የውጭ አገር ሰዎችን ጋብዘው ሆቴሉን አስመረቁ:: የመጀመሪያው ሥራ አስኪያጅም ሙሴ ፍሬደሪክ ሐል ነበር:: በኃላ ግን አቶ ዘለቃ አጋርደው ተሾሙ::
እንደ አገር አባባል ጣይቱ እጅ የሚያስቆረጥም ወጥ እያሠሩ ገበያ ቢጠብቁ ጠፋ:: እንኩዋን ምግብ መብላት ከግሪኮቹ ሻይ ቤት ገብቶ ሻይ መጠጣት ነውር ነበረና: ጣይቱ ጠዋት የሚያሠሩት ወጥ ለሠራተኞቹ የማታ ራት ይሆን ጀመር:: የሚስታቸው ገበያ ማጣት ያሳሰባቸው አጤ ምኒልክ አንድ ቀን ከችሎት ሊነሱ ሲሉ በአካባቢያቸው ላሉ መኩዋንንቶች "ጣይቱ ምግብ የሚሸጥበት ቤት ከፍታለችና ኑ እንሂድና ልጋብዛችሁ" ብለው ወሰዱዋቸው:: መኩዋንንት በላ ጠጣና ምኒልክ 30ብር ከፈሉ::
በማግሥቱ እንደተለመደው ገበያ ቢጠበቅ ጠፋ:: ቀጥሎም ጠፋ; ቀጥሎም ጠፋ:: እንደገና ምኒልክ ሆቴል ገብቶ መብላት ነውር ያለ መሆኑን ለመኩዋንንቱ ገልፀው እንደገና ምሣ ጋበዙ:: በሌላው ቀን አሁንም ገበያ አልተገኘም:: ቢጠበቅ ቢጠበቅ ድርሽ የሚል ሰው ጠፋ:: በሌላ ቀን ደግሞ አጤ ምኒልክ ከችሎት ሊነሱ ሲሉ በዙሪያቸው ላሉ መኩዋንንት "ሰማችሁ ወዳጆቼ" አሉ:: "በፈረንጅ አገር አንድ ቀን አንድ ሰው የጋበዘ እንደሆነ ያ የተጋበዘ ሰው በሌላ ቀን ደግሞ ብድሩን ይከፍላል ብድሩን ካልከፈለ ግን እንደ ነውር ይቆጠርበታል:: "ብለው ንግግራቸውን ሳይጨርሱ መኩዋንንቱ "እርስዎን ፈርተንና አፍረን ነው እንጂ የሚሆንልን ከሆነ የምኒልክን ብድር ለመመለስ እኔ አለሁ" እያለ ተራ በተራ ከሆቴል ቤት ምኒልክንና ጣይቱን ይጋብዝ ጀመረ:: ገበያ እየደራ ሄደ:: ምሳችንን እቴጌ ሆቴል ሄደን እንብላ የሚለው ስለበዛም ስሙ እቴጌ ሆቴል ተባለ::

ጳውሎስ ኞኞ
አጤ ምኒልክ መፅሐፍ
Meseret Assefa's photo.
Meseret Assefa's photo.
Meseret Assefa's photo.

No comments:

Post a Comment