Friday, January 30, 2015


ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ በአቶ ትዕግስቱ ለሚመራው የአንድነት ፓርቲ እና በአቶ አበባው ለሚመራው መኢአድ ፓርቲ ዕውቅና ሰጠ
የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ጽህፈት ቤት በአመራር ውዝግብ ውስጥ በነበሩት አንድነት ለፍትህ እና ለዴሞክራሲ ፓርቲና በመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ዙሪያ ውሳኔ አሳልፏል።
አንድነትን በተመለከተ አቶ ትዕግስቱ አወሎ የፓርቲው ህጋዊ ሊቀመንበር ናቸው ብሏል። በመኢአድ በኩል ደግሞ ለአቶ አበባው መሃሪ የህጋዊ ፕሬዚዳንትነት ዕውቅና ሰጥቷል።
አንድነትም ሆነ መኢአድ ቦርዱ ዕውቅና በሰጣቸው መሪዎች እየተመሩ በምርጫው መሳተፍ እንደሚችሉም ነው የተወሰነው።

መግለጫውን የሰጡት የኢትዮጵያ ብሄራዊ ምርጫ ቦርድ ዋና ፀሃፊ አቶ ነጋ ዱፌሳ ቦርዱ ለሁለት የተከፈሉትን የሁለቱንም ፓርቲዎች አመራር ችግራቸውን ለመፍታት የተሰጣቸውን ጊዜ ለመጠቀም ያከናወኗቸውን ተግባራት በጥልቀት መመርመሩንም ተናግረዋል።
ቀደም ሲል የብሄራዊ ምርጫ ቦርድ አንድነትና መኢአድ በውስጣቸው የተከሰተውን ችግር ፈትተው እንዲመጡ የ14 ቀናት ጊዜ ሰጥቶ የነበረ ሲሆን ቦርዱ የጊዜውን መጠናቀቅ ተከትሎ በቀጣዮቹ ሁለት ቀናት የመጨረሻ ውሳኔ ለማሳለፍ በዛሬው ዕለት ቀጠሮ መያዙ ይታወሳል።

No comments:

Post a Comment