Sunday, February 1, 2015

ባቡሩ... የሚያገናኝ ነው የሚያለያይ!

ባቡሩ... የሚያገናኝ ነው የሚያለያይ!
ድሮ ድሮ ድልድይ በሌለባቸው የገጠር አካባቢዎች በክረምት ሰዎች እርስ በርስ ለመገናኘት ዙሪያ ጥምጥም ይዞሩ ነበር። የአንድ ቀኑን መንገድ ውሃ ሙላት በሚሆንበት የክረምት ወቅት ሶስት እና አራት ቀን ይፈጅባቸዋል።
አሁን በመሃል አዲሳባ ማዶ ለማዶ ሆነው ቡና ይጣጡ የነበሩ ሰዎች ባቡሩ አቆራርጧቸዋል። የተሰራልን ባቡሩ የከተማ ቀላል ባቡር /ትራም ሲሆን መንገዱ ደግሞ በምኒሊክ ዘመን የሚሰራው አይነት ለከባድ ባቡር የሚሆን ከከፍለ ሀገር ክፍለ ሀገር የሚያገናኘው ነው።
ለምሳሌ ያክል፤ እኔ በምኖርባት ማንችስተር ፕራም ወይም የከተማ ቀላል ባቡር ሲሄድ እንዳትጠጉኝ፤ ብሎ መንገድ አጥሮ ሰውን ከሰው አለያይቶ አይደለም።
ለማነጻጸሪያ ይሆን ዘንድ እነሆ የሁለቱም ቀላል ባቡር ሰዕሎች።
እኔ የምለው መሃንዲሱ አዲሳባዬን እንዲህ ግርድፍድፏን ከማውጣቱ በፊት ምናለበት ደውሎ ቢጠይቀኝ፤ ቢያንስ ቢያንስ ይቺን የማንችስተር ቀላል ባቡር ፎቶግራፍ አንስⶬ የማልከለት ሆኜ ነው! የምር ግን እንዲህ ሰፈርተኛውን ማዶ ለማዶ የሚያለያይ ባቡር ግንባታ ከመስራት በፊት ምናለበት የሌሎች ሀገሮችን ልምድ... ቀላል ባቡር አሁን ያለበት ቴክኖሎጂን ቃኘት ቃኘት ማድረግ ቢችሉ!
በመጨረሻም፤
ዛሬ ባለስልጣኖቹ በባቡሩ ላይ ተሳፍረው ሲመርቁ ስመለከታቸው ግን አንድ ነገር ጭንቅቅቅ አለኝ። ሰዎቹ ወራጅ ማለት ስለሚጨንቃቸው እዛው ባቡሩ ላይ ቁጭ በለው ይቀሩ ይሆን... ወይስ ደፍረው ወራጅ ይሉ ይሆን... እኔ የባቡሩ ሹፌር ወይም አስተናጋጁ ብሆን ... ልክ ሲወረዱ... አይዟችሁ ወረዱ... ምንም አይላችሁም... ወረዱ.... ኧረ... ውረዱ... እያልኩ አበረታታቸው ነበር!

No comments:

Post a Comment