Wednesday, November 16, 2016

የድንገተኛ አዋጁን ተከትሎ የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች እየታሰሩ ይገኛሉ።

በአገሪቱ የተለያዩ ክፍሎች ተስፋፍቶ የነበረውንና በዋና ከተማዋ በአዲስ አበባ ባሉ አቅራቢያ ከተሞች ተከስቶ የነበረውን ህዝባዊ አመፅ ለማብረድ መንግስት መስከረም 29፣2009 ዓ.ም ያወጣውን የድንገተኛ ጊዜ አዋጅ ተከትሎ የተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲ አባላት በፖሊስ ከያሉበት እየታደኑ እስር ቤት መግባታቸውን የተለያዩ መረጃዎች ያመለክታሉ። ይህን ተከትሎ በቅርቡ የሰማያዊ ፓርቲ የሴቶች ጉዳይ ሃላፊ ሆና የተመረጠችው ወጣት ብሌን መስፍን፣ የሰማያዊ ፓርቲ ምክር ቤት ሰብሳቢ ይድነቃቸው ከበደ፣ እንዲሁም በ2007 ዓ.ም ምርጫ ሰማያዊ ፓርቲን ወክሎ ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እጩ ተወዳዳሪ የነበረው እያስጴድ ተስፋዬ ከያሉበት ተይዘው በተለያዩ ፖሊስ ጣቢያዎች ይገኛሉ። የቀድሞው አንድነትና ፍትህ ፓርቲ የኦዲትና ኢንስፔክሽን ሀላፊ እንዲሁም የምክር ቤት አባል የነበረው ዳዊት ተሰማም በእስር ላይ ይገኛል። ባለፈው ሳምንት መጨረሻ ደግሞ የዞን9ኙ ጦማሪ በፍቃዱ ሃይሉ ይህንን ዝርዝር ተቀላቅሏል፡፡ በፍቃዱ ለአሜሪካን ድምጽ ሬዲዮ አስቸኳይ ጊዜ አዋጁን አስመልክቶ የሰጠውን አስተያየት ተከትሎ በኮማንድ ፓስቱ ትፈለጋለህ በመባል ለእስር የበቃው
  – የሰማያዊ ፓርቲዋ ብሌን መስፍን በተፈታች በሰአታት ልዩነት ውስጥ ዳግም በፖሊስ ቁጥጥር ውስጥ ውላለች። እያስጴድ ተስፋዬና ይድነቃቸው ከበደ እና በፍቃዱ ሃይሉ ፍርድ ቤት አልቀረቡም
የሰማያዊ ፓርቲ የሴቶች ጉዳይ ሃላፊ ሆና የተሾመችው ብሌን
መስፍን በተፈታች በሰአታት ውስጥ በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውላለች። የአስቸኳይ ጊዜ ድንገተኛ አዋጁ በፀደቀ በ 2ኛው ቀን ማለትም ከጥቅምት 01/2009 ዓ.ም ጀምሮ በእስር ላይ የነበረቸው ብሌን መስፍን በጥቅምት 08 የመናገሻ ፍርድ ቤት 10ሺ ብር ዋስትና አስየዛ እንድትወጣ ውሳኔ ቢያስተላልፍም የላዛርስት ፓሊስ ጣብያ መርማሪዎች ሰባራ ባቡር የሚገኘው የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት በመውሰድ የስር ፍርድ ቤት ያስተላለፈው የዋስትና መብት ላይ ይግባኝ በማለት “ተጠርጣሪዋ የተጠረጠረችበት ወንጀል ሁከትና አመፅ ማነሳሳት ስለሆነ ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ ይሰጠኝ” ብሎ በመጠየቁና ፍርድ ቤቱም ይገባኙን በመቀበሉ ለተጨማሪ ቀናት በእስር እንድትቆይ ተደርጓል። ፖሊስ “የሷን ጉዳይ ኮማንድ ፖስቱ ነው የሚያየው” በማለት በተደጋጋሚ የምርመራ ጊዜ ቀጠሮ እስዲሰጠው ቢጠይቅም ፍርድ ቤቱ በጥቅምት 25 በዋለው ችሎት አስይዛ የነበረው 10ሺ ብር ዋስ ተጠብቆላት ከእስር እንድትፈታ አዟል። ብሌን መስፍን ከተፈታች በኋላ እቤትዋ ገብታ ምግብ በመመገብ ላይ እያለች ፖሊሶች መጥተው ወደ ፖሊስ ጣብያ ወስደዋታል። የታሰረችበት ምክንያት ይሄ ዘገባ እስከተጠናከረበት ሰአት ድረስ አልታወቀም፤ ፍርድ ቤትም እስከአሁን አልቀረበችም። በሌላ በኩል የሰማያዊ ፓርቲ አመራር የሆኑት እያስጴድ ተስፋዬና ይድነቃቸው ከበደ በእስር ላይ የሚገኙ ሲሆን እስከአሁን ድረስ ፍርድ ቤት አልቀረቡም። ከስራ በመውጣት ላይ እያለ መገናኛ አካባቢ በቁጥጥር ስር የዋለው እያስጴድ ተስፋዬ አምቼ አካባቢ የሚገኝ ፖሊስ ጣብያ የታሰረ ሲሆን ከቤተሰቦቹ ውጭ ማንም እንዲጠይቀው እንዳልተፈቀደ ታውቋል። ሌላው የሰማያዊ ፓርቲ የምክር ቤት ሰብሳቤ ይድነቃቸው ከበደ መርካቶ አካባቢ የሚገኘው 4ኛ ፖሊስ ጣብያ በእስር ላይ የሚገኝ ሲሆን ፍርድ ቤት እስካሁን አልቀረበም። የኢትዮጵያ መንግስት ባወጀው ድንገተኛ አዋጅ ምክንያት ፖሊስ ወይም የፀጥታ ሀይል ተጠያቂነት የማያስከትል ስልጣን የተሰጠው ሲሆን ማንኛውንም ግለሰብ አስሮ እስከፈለገው ጊዜ ድረስ ማቆየት ይችላል። ባለፈው ሳምነት መጨረሻ ይህንኑ ተከትሎ የታሰረው የዞን9ኙ ጦማሪ በፍቃዱ ሃይሉም በተመሳሳይ ፍርድ ቤት ሳይቀርብ ለቀናት ታስሯል፡፡

No comments:

Post a Comment