Friday, January 1, 2016

ኤርትራን ፕሬስ የተባለ ድረገጽ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋን የዓመቱ ምርጥ ሰው አድርጎ መረጠ

በሳምንት ከ600, 000 በላይ አንባቢዎች እንዳሉት የሚገልጸው ኤርትራን ፕሬስ የተሰኘው የመረጃ መረብ የ2015 ዓ.ም ፕሮፌሰር ብርርሃኑ ነጋን የዓመቱ ምርጥ ሰው አድርጎ መረጠ::
ከጁላይ 2015 ጀምሮ የኢሕ አዴግን መንግስት ለመጣል ኤርትራ ጠቅልለው መግባታቸውን የገለጸው ድረገጹ እንዲህ ያለውን ውሳኔ በመወሰናቸውና ትግሉን ለመምራት ያላቸውን ብቃት በመተንተን የዓመቱ ምርጥ ሰው ብሏቸዋል::

ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ የ2007 ዘ-ሐበሻ አንባቢዎች የዓመቱ ምርጥ ሰው ተብለው መመረጣቸው የሚታወስ ሲሆን በወቅቱ ስለርሳቸው የሚከተለውን ጽፈን ነበር::
ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ በ1958 ዓ.ም ደብረዘይት አካባቢ የተወለዱ ሲሆን ምንም እንኳ የተወለዱት ከሃብታም ቤተሰብ ቢሆንም አስተዳደጋቸው ግን ራሳቸውን ችለው እንዲያድጉ እየተማሩ ነው:: ይህንን ፕሮፌሰር ብርሃኑ በሃገር ቤት ለሚታተም ጋዜጣ በ1997 ዓ.ም ሲናገሩ “አባቴ ነጋ ቦንገርን ልጅ እያለሁ ሲኒማ ራስ ጥሩ የህንድ ፊልም ወጥቶ ለማየት ሳንቲም ስጠኝ ስለው ራስህ ሰርተህ ስታገኝ ትገባለህ ይለኝ ነበር” (ቃል በቃል የተወሰደ አይደለም) ይላሉ:: አባታቸው አቶ ነጋ ቦንገር ሲያሳድጓቸው በማሞላቀቅ ሳይሆን ራሳቸውን መቻል እንዳለባቸው በማስተማር ነበር:: ይህም ለፕሮፌሰሩ ስኬት ጠቅሟቸዋል::
ፕሮፌሰሩ ወደ ሳሪስ አካባቢ ግሎባል የሚባል ደረጃውን የጠበቀ ሆቴል ከፍተው የነበረ ቢሆንም በሽብርተኛነት በኢትዮጵያ መንግስት ከተከሰሱ በኋላ ይህ ሆቴል ተወርሷል::
ፕሮፌሰር ብርሃኑ ወደ ትግሉ ዓለም የገቡት ገና የ17 ዓመት ወጣት በነበሩበት ወቅት ነው:: ያን ጊዜ ከኢህ አፓ ጋር በሚሰሩበት ወቅት ብዙ ምስጢሮች ባይነገራቸውም መኪና ይነዱ ስለነበር የኢሕአፓ አመራሮችን ከቦታ ቦታ በመውሰድ አገልግሎት ይሰጡ እንደነበር አብረዋቸው ይታገሉ የነበሩ ሰዎች ለዘ-ሐበሻ ይናገራሉ:: እንዲሁም ፕሮፌሰር ብርሃኑ በወቅቱ በኢህአፓ አመራሮች እርምጃ ሊወሰድባቸው ሲል በሱዳን በኩል አምልጠው እንደጠፉ ከታሪካቸው ያሰባሰብነው መረጃ ያመለክታል::
በሱዳን በኩል አድርገው አሜሪካ ከገቡም በኋላ ትምህርታቸው ላይ በማተኮር በከፍተኛ ማዕረግ የተመረቁ ሲሆን ኢህአዴግ አዲስ አበባን ከተቆጣጠረ በኋላ ኢትዮጵያ ጠቅልለው በመግባት ሃገራቸውን ማገልገል ጀምረዋል:: ፕሮፌሰር በቅድሚያ ኢሕ አዴግን ለመለወጥ አዳዲስ ሃሳቦችን ቢያቀርቡም ኢህ አዴግ ግን የሚለወጥ ድርጅት ሊሆን አልቻለም:: በዚህም ተስፋ ሳይቆርጡ የኢትዮጵያ የኢኮኖሚክስ ባለሙያዎች ማህበርን በመመስረት ብዙ አስተዋጽኦ አበርክተዋል::
ከምርጫ 2007 በፊት ፕሮፌሰር ብርሃኑ እና ፕሮፌሰር መስፍን በብሄራዊ ሎተሪ አዳራሽ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን በመሰብሰብ ስለ ነፃነትና መብት ምንነት በሰፊው በሕዝባዊ ስብሰባ ይሰብኩ ነበር:: በርካታ ተከታዮችን እያፈሩ መምጣታቸው ያስፈራው መንግስት ሁለቱንም ታዋቂ ፖለቲከኞች ሕገመንግስቱን በኃይል ለመናድ በሚል አስሮ ሲያንገላታቸው ቆይቷል::
ምርጫ 1997 እየቀረበ ሲመጣ በየወሩ በሂልተን ሆቴል ኢትዮጵያ በ2020 በሚል ምሁራን እየተሰባሰቡ ኢትዮጵያ በ2020 ዓ.ም ምን መሆን እንዳለባት እንዲመካከሩ ያደርጉ የነበሩት ፕሮፌሰር ብርሃኑ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህር በነበሩበት ወቅት ደመወዛቸውን ለችግረኛ ተማሪዎች ያከፋፍሉ እንደነበር ይነገራል::
ፕሮፌሰሩ ቀስተዳመና የተሰኘ ፓርቲ አቋቁመው ከኢድሊ ጋር በመተባበር ታላላቆቹን መኢአድና ኢዴፓ-መድህንን አንድ በማድረግ ቅንጅት ፓርቲ እንዲፈጠርና በምርጫ 97 ኢትዮጵያ ውስጥ ትልቅ ለውጥ እንዲፈጠር ጥረው ነበር:: በዚህም የአዲስ አበባ ከንቲባ ሆነው በሕዝብ ተመርጠው የነበረ ቢሆንም መንግስት በሃይል ያመጣሁትን ስልጣን በስኪብርቶ አለቅም በሚል የፖለቲካውን ምህዳር ዘግቶታል::
በዚህ ምርጫ ሰብሰብም ፕሮፌሰር ብርሃኑ እስር ቤት ተወርውረው ነበር:: ከ እስር ቤት ከወጡ በኋላም ሰላማዊ ትግል ብቻውን ለውጥ አያመጣም በሚል ወደ ሁለገብ ትግል በመሸጋገር ግንቦት 7ን መሰረቱ:: ግንቦት ሰባት በአሁኑ ሰዓት ከተለያዩ ድርጅቶች ጋር እየተዋሃደ ትግሉ ወደ አንድ አቅጣጫ እንዲሸጋገር ፕሮፌሰር ብርሃኑ ሰርተዋል::

No comments:

Post a Comment