Wednesday, August 24, 2016

ሕዝባችን እይተቀጠቀጠ በሄደ ቁጥር ይበልጥ ይጠብቃል!! August 24, 2016


def-thumb
ኢትዮጵያን ላለፉት 25 ዓመታት አፍኖ የሚገዛው ሕወሐት ብዙ ጊዜ ለቆዩና ሕዝቡን ላንገሸገሹት ችግሮች መፍትሔው ይበልጥ ማፈን መቀጥቀጥና ጥያቄዎቹ እንዳይነሱ ማዳፈን እንደመፍትሔ ቆጥሮታል። በመላ ሀገሪቱ ዙሪያ ሰላማዊ ጥያቄ እንስተው ባዶ እጃቸውን አዳባባይ ለወጡ ወገኖቻችን ሁሉ መልሱ በጥይትና በዱላ መጨፍጨፍ ከሆነ ስንበተ። የህወሀት አምባ ገነኖች ስልጣንና በስልጣን ያገኙት የዝርፊያ ጥቅም አሳውሮ ግድግዳ ላይ የተጻፈ ግልጽ ነገር ማንበብ እንዳይችሉ አድርጓቸዋል። ግድግዳው ላይ የተጻፈው ጽሑፍ የአፈና የዝርፊያ ይማጭበርበርና በህዝብ ደም እየጨቀዩ የሚኖርበት ዘመን በምድረ ኢትዮጵያ እያከተመ መሆኑን ይናገራል። ብዕብሪት የታወረ አይናቸው ግን ሊያየው አልቻለም።

ባለፈው ሳምንት መጨረሻ ላይ ያዲስ አበባ ነዋሪ በሰልፍ ወጥቶ ብሶቱንና ጥያቄውን ለማቅረብ ዝግጅት ላይ መሆኑን የተረዳው የህወሐት አገዛዝ የመረጠው ህብረተሰቡ ከቤቱ እንዳይወጣ በመላው ከተማ ሰራዊትና ነጭ ላባሽ አሰማርቶ ማፈን ነበር። ሕወሀት ገልቱ ስለሆነ እንጂ ለራሱም ሆነ ለአጋሮቹ
የሚጠቅመው ሰላማዊ ጥያቄውንና የተቃውሞውን ምክንያት ከሕዝቡ በቀጥታ መስማት ነበር። አፈናው የሕዝቡን አብሮ የሚጮህ ድምጽ አስቁሞ እንደሆን እንጂ ብሶቱንና ለለውጥ ያለውን ፍላጎትና ተነሳሽነት እንዳላስቆመውማ የታወቀ ነገር ነው። የሕዝብ ብሶት ድምጽና ጭስ መውጫ አያጣም። ሕወሀቶች አዲስ አበባን አፍኖ በመዋል ያገኙት የመሰላቸውን እፎይታ ሪዮ ኦሎምፒክ መንደር ሄደው ሊያፍኑት አልቻሉም። ጀግናው አትሌት ፈይሳ ሌሊሳ በአለም ዙሪያ ማዕበል ያስነሳ በሚመስል ደረጃ ወያኔ በውሸት የገነባውን የረጅም ጊዜ የተቀባባ ገጽታ ባንድ ጀምበር ፍርክስክሱን አውጥቶት ነው ያደረው።

ወያኔ ያልገባውና እንዲገባው ያልፈለገው ነገር የህዝቡ ብሶትና ለመብቱ መነሳሳት ብልጭ ድርግም ከማለት አልፎ የማያቁዋርጥ ማዕበል እየሆነ በመሄድ ላይ ያለ መሆኑን ነው። ይህ ትግል በጉልበት ማስቆም ከሚቻልበት ደረጃ ብዙ አልፏል። ይልቁንም ወያኔ ከፋፍያቸዋለሁ ብሎ የነበሩ ማህበረሰቦች ሳይቀሩ ሀይላቸውን እያስተባበሩ የመጡበት ሁኔታ ተፈጥሯል። ይህን ትግል ከዳር እንዳይደርስ የሚያደርግ ሰብዓዊ የአፈና ሀይል ፈጽሞ ሊኖር እንደማይችል የሚያሳዩ ምልክቶች እየበረከቱ መታየት ጀምረዋል። እያንዳንዱዋ የአፈና ሙከራ የህዝቡን ሐይል የበልጥ እያጠናከረችው እንደምትመጣም ሳይታለም የተፈታ ነው።
ዛሬ ሙሉ ለሙሉ በሚባል ሁኔታ ኢትዮጵያ በወያኔ ሰራሽ አደጋ ውስጥ ወድቃለች። ወያኔ ሕዝብ ተሰብስቦ በተቃወመው ቁጥር የሚታየው ስልጣኑንና በስልጣኑ ምክንያት የሚፈነጭበትን የዘረፈውን የሀገሪቱን ሀብት ላጣ እችላለሁ የሚለው ፍራቻ ብቻ ሆኗል። ችግር የሚፈታበትን የፖለቲካ ዘዴ የመፈለጊያ ፍላጎቱንም አቅሙንም አጥቷል።የህዝብ ብሶትና ድምጽን ባፈና ማቆም እንደማይቻል ከሚያየው ነገር እንኩዋን መማር ተስኖታል። ሀገሪቱን የመጠበቅና እንድነታችንን የማኖር ሀለፊነት ከመቼውም በበለጠ ዛሬ በራሳችን በሀገሪቱ ዜጎች እጅ ላይ ቀድቋል። እንዳንድ ተራ አምባገነኖች የሚያሳዩትን ትንሽ ነገር እንኩዋን ከሀገሪቱና ከህዝቡ ጥቅም አንጻር ለማየት ፈቃደኛ ያልሆነ ምንም ሀለፊነት የማይሰማው የአጋሰሶች ስብስብ ነው ኢትዮጵያን እየመራ ያለው የህወሀት ጉጅሌ።
እንደዚህ ፈጽሞ ሀላፊነት የማይሰማው የወሮበሎች ቡድን በነገሰበት ሀገር ውስጥ ሀገር የማኖርና የህዝብን እንድነት የመጠበቅ ትልቁ ሀላፊነት ያለው በህዝቡና በህዝባዊ ሀይሎች ላይ መሆኑ ሳይታለም የተፈታ ነው። ወያኔ ጥቅሙንና ስልጣኑን ለማስጠበቅ ሊያደርግ የማይችለው ቆሻሻ ስራ ይኖራል ብሎ ማሰብ አይቻልም። ሌላው ቀርቶ ብሔረሰቦችን እርስበርስ በማጋጨት አጀንዳውን ለማስቀየስ ባደባባይ ሳይቀር ብዙ እየሰራ እንደሆነ እየተመለከትን ነው። ከዚህ የባሱ የተንኮል ስራዎች ህብረተሰቡ ውስጥ ለመስራት ወደኋላ እንደማይል ጠንቅቀን በማወቅ ትግላችንን ይበልጥ እያስተባበርን መሄድ የግድ ይለናል።
አርበኞች ግንቦት 7 ከዚህ ትግል መህል እንጂ ዳር የቆመ ሀይል አይደለም። በሀገሪቱ ማንኛውም ክፍል ባሉ የህዝቡ ተጋድሎዎች ውስጥ አስከመጨረሻው አለን። እኛም ህዝቡ ነንና ከህዝቡ አንለይም። የሕዝባችንን ሞት ሞተን ለነጻነቱ ከሚያደርገው ትግል ጎን፤ ፊትና ሁዋላ እንዳለን ጠላትም ወዳጅም እንዲረዳው ያስፈልጋል።
ለወያኔ ከፋፋይ ፖለቲካ ሳንበገር ሀይላችንን ይበልጥ እያስተባበርን እንነሳ። የነጻነት ቀናችን ከትናንት ዛሬ ቅርብ ነውና።
የወያኔ አፈና እየበረታብን በሄደ ቁጥር ይበልጥ እየጠነከርን እንደምንሄድ እርግጠኞች ነን።
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!!

No comments:

Post a Comment