Monday, June 6, 2016

“ከ500 በላይ የኦሮሞ ወንድሞቻችን ሲገደሉ ከ30ሺህ በላይ እስር ቤት ሲታጎሩ ዓለም እንዳልሰማ ዝም ብሏል፤ ከነጮቹ ምንም መጠበቅ የለብንም” ፕ/ር ብርሃኑ ነጋ


ትናንት በኖርዌይ አርበኞች ግንቦት 7 የተሳካ የገቢማሰባሰቢያ ዝግጅት አድርጎ ከ2 ሚሊዮን ብር በላይ ተሰብስቧል:: በዚህ ስብሰባ ላይ የተገኙት የንቅናቄው መሪ ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ ያደረጉትን ንግግር ጌታቸው በቀለ እንደሚከተለው ጨምቆ አሰናድቶታል::
መድረኩን እና አድማጫቸውን ለሰዓታት በጉጉት ወጥረው የመያዙ አቅም ያላቸው ድምፀ ጎርናናው ፕሮፌሰር ብርሃኑ ንግግራቸውን የጀመሩት ወደ ኦስሎ ከመጡ በኃላ ወዲያው ያደረጉት ከኖርዌይ ባለስልጣናት ጋር በኖርዌይ ስለሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች ጉዳይ መነጋገራቸውን እና ለኖርዌዮች ሊረዱት ይችላሉ ባሉት መንገድ ስለ ኢትዮጵያ ችግር ያስረዱበትን መንገድ አብራርተዋል።በመቀጠል የንግግራቸው ዋና ፍሬ ሃሳብ ስለነበረው የኢትይጵያን የአሁኑን የወያኔ ስርዓት ከፈረሰው የደቡብ አፍሪካ የዘር-መድሎ ስርዓት ጋር ያለውን ተመሳሳይነት፣የባሰ የሆነበትን መንገድ እና የትግል ስልቶቹን ዝምድና በሚገባ አብራርተዋል።

የደቡብ አፍሪካ የፈረሰው የዘር መስሎ ሥርዓት እና የወያኔ ስርዓት አንድነት እና ልዩነት
ፕሮፌሰር ብርሃኑ ነጋ የደቡብ አፍሪካን የዘር መድሎ ስርዓት የሚመሳሰልባቸውን ሁለቱ የስልት መንገዶች እንዲህ አብራርተዋል።
1ኛ/ የስነ-ልብና ጦርነት በብዙሃኑ ላይ ማድረግ

ነጮች ጥቂቶች ነበሩ።ታድያ እንዴት ብዙሃኑን ጥቁሮች እረግጠው ገዙ? ብለው ከጠየቁ በኃላ መልሱ የነጮች በጥቁሮች ላይ ያደረጉት የስነ-ልቦና ጦርነት አንዱ መሆኑን ሲያብራሩ ጥቁሮችን መጀመርያ ያደረጉት ጥቁሮች እኔ ለነፃነት ብቁ ነኝ እንዴ ? ብለው እራሳቸውን እንዲጠይቁ እና አለመሆናቸውን እንዲያስቡ የተደረገ የስነ-ልቦና ተፅኖ መኖሩን አብራርተው በተመሳሳይ ደረጃ ወያኔ በሕዝቡ ላይ ለነፃነት ብቁ እንዳልሆነ የረቀቀ የስነ-ልቦና ዘመቻ እንደሚያደርጉ አብራርተዋል።
2ኛ/ በጎሳ መከፋፈል
በደቡብ አፍሪካ ዘረኛው መንግስት አንዱ የተጠቀመበት መንገድ እራሳቸው ጥቁሮችን በጎሳ መከፋፈል እርስ በርስ እንዲጋጩ ማድረግ ነበር።በተመሳሳይ መንገድ ወያኔም እየሰራበት እንደሚገኝ ገልጠው የደቡብ አፍሪካ ትግልም እነኝህን ችግሮች አስታኮ ትግሉን በሶስት መንገዶች መቅረፁን አብራርተዋል።
የደቡብ አፍሪካ የነፃነት ትግል ሶስቱ የትግል መንገዶች
ፕሮፌሰር ብርሃኑ የደቡብ አፍሪካ ትግል የተከተላቸው መንገዶች ሶስት እንደነበሩ አብራርተዋል። እነርሱም:
ሕዝባዊ እምቢተኝነት በአገር ውስጥ፣
ሕዝባዊ እምቢተኝነት በውጭ አገሮች እና
በማንዴላ የሚመራው የመሬት ላይ የትጥቅ ትግል የሚሉ ነበሩ።
የደቡብ አፍሪካ ትግል ከላይ የተጠቀሱትን መንገዶች ይያዝ እንጂ የአገር ውስጡ ሕዝባዊ እምቢተኝነት ግቦቹ ሁለት ነበሩ። እነርሱም መጪዋ ደቡብ አፍሪካ በዜግነት ላይ የተመሰረተች ትሆናለች የሚል እና አንድ ሰው አንድ ድምፅ ይኖረዋል የሚሉ ነበሩ። የውጭው ሕዝባዊ እምቢተኝነት በተለይ አለምን ያነቃነቀ እና ዋና ትኩረቱ በዓለም ላይ ያሉ ታላላቅ ኩባንያዎች በደቡብ አፍሪካ ኢንቨስት በማድረግ የዘር-መድሎ ስርዓቱን እንዳይደግፉ ማድረግ ነበር። ሆኖም ግን ዓለም አቀፍ ኩባንያዎች ይህንን ሁሉ በደል እያዩ ደቡብ አፍሪካ ላይ ከፍተኛ መዋለ ንዋይ ያፈሱ ነበር። ሶስተኛው የትጥቅ ትግሉ ከጎረቤት አገሮች በመነሳት የደቡብ አፍሪካን ዘረኛ መንግስት ሰላም የመንሳት አላማ ነበረው። ይህ ትግል በተለይ በደፈጣ ውግያ የደቡብ አፍሪካውን ስርዓት ሰላም የነሳ እና ከጎረቤት አገራቱ ጋር ከፍተኛ ውጥረት ውስጥ የገባበት ነበር።
ፕሮፌሰር ብርሃኑ የሶስቱን የደቡብ አፍሪካ የትግል ስልት ካነሱ በኃላ ከሶስቱ የትኛው የተሻለ ስልት ነበር? የትኛውስ የበለጠ አስተዋፅኦ አደረገ? በማለት ከጠየቁ በኃላ መልሱን ሲመልሱ አንዳቸው ከአንዳቸው ይበልጣሉም ያንሳሉም ማለት እንደማይቻል አብራሩ። ሶስቱም እርስ በርስ ተደጋግፈው ነው ውጤት ያመጡት።በውጭ ያለውን ድጋፍ በማስቆም የአገር ውስጡን እምቢተኝነት መደገፍ ተችሏል።በትጥቅ ትግሉ እረፍት ነሺነትም ለድል መቃረብ ተችሏል በማለት የደቡብ አፍሪካን ሁኔታ ከገለጡ በኃላ ከእኛ ጋር ያለውን ልዩነት እና አንድነት እንዲህ አብራርተዋል።

የወያኔ ስርዓት እና የደቡብ አፍሪካ የዘር መድሎ ስርዓት ተመሳሳይነት
የወያኔ ስርዓት የደቡብ አፍሪካው ስርዓት ያለው አንድነት ሁለቱም መሰረታቸው በዘር ላይ የተመሰረተ መሆኑ፣በምጣኔ ሀብት፣ፖለቲካውን እና ያዩትን ሁሉ ለመቀራመት ያላቸው ፍላጎት እና በሕዝብ ላይ የሚደርሰው ግድያ ፣እስር በዋነኛነት ይገለጣል።በእዚህ ተመሳሳይ ለትግሉ በእኛ በአርበኞች ግንቦት 7 በኩል የቀየስነው የትግል ስልትም ሶስቱን ማለትም ሕዝባዊ እምቢተኝነት በአገር ውስጥ፣ ሕዝባዊ እምቢተኝነት በውጭ አገር እና መሬት ላይ የሚደረግ የትጥቅ ትግል የሚሉት ናቸው። ሶስቱም አንዳቸው ከአንዳቸው ተደጋግፈው የሚሄዱ መሆናቸውን በሰፊው አብራርተዋል።
የደቡብ አፍሪካ የዘር መድሎ ስርዓት ከወያኔ የተሻለባቸው መንገዶች
ፕሮፌሰር ብርሃኑ የደቡብ አፍሪካ ዘረኛ ስርዓት ከወያኔ የሚለይባቸው እና የተሻለባቸው መንገዶችን እንደሚከተለው አብራርተዋል።
ሀ/ በደቡብ አፍሪካ ስርዓቱ አፓርታይድን በሕግነት አውጥቶ ስለ አወጣው ሕግ ይከራከራል እንጂ ያወጣውን ሕግ ሰርዞ ወይንም የሌለ ሕግ ትጠቅሶ አይከራከርም ነበር። በደቡብ አፍሪካ አፓርታይድ በሕግ ተደንግጎ ነበር። ስለሆነም ስርዓቱ የቆመው ላወጣው ሕግ ነበር።ወያኔ ግን ያወጣውን ህገ መንግስት በመጣስ ሕግ የሚያሰቃይ ነው
ለ/ የደቡብ አፍሪካ ስርዓት ስለ ውደፊቷ ደቡብ አፍሪካ ይወያይ ነበር።ቢያንስ ወደፊት የጎደለውን ማሟላት ያለባት ደቡብ አፍሪካ መኖር አለባት በማለት በእስር ቤት ከሚገኙት ማንዴላ ጋር ማቆምያ የሌለው ግን እስር ቤት እየሄደ ይወያይ ነበር።ይህ ማለት ስለተባበረች ደቡብ አፍሪካ መጨነቅ ነበር። የወያኔን ስርዓት ብትመለከቱ ስለ ወደፊቷ ኢትዮጵያ የሚባል ራእይ የላቸውም።ስለመተባበር፣ህብረት ወዘተ ምንም የማይጨነቁ ናቸው።
ሐ/ በደቡብ አፍሪካ የፍትህ ስርዓቱ ላይ መንግስት እጁን አያስገባም። ይልቁንም መንግስት ብዙ ጊዜ የተረታባቸው አጋጣሚዎች ነበሩ።ይህ ብቻ አይደለም የአፓርታይድ ስርዓት ከበርካታ የሰራተኛ ማኅበራት ጋር የገጠሙት አመፆች የሰራተኛ ማኅበራቱ የነበረውን የሕግ ስርዓት ተንተርሰው ስለሚንቀሳቀሱ ነው። የወያኔ ስርዓት ስትመለከቱ የፍትህ ስርዓቱን በሙሉ ደምስሶ በእራሱ የያዘ እና መቀለጃ ያደረገ ነው።ተመልከቱ! ከደቡብ አፍሪካ አፓርታይድ ስርዓትም ምን ያህል የከፋ ስርዓት ላይ እንደሆንን።
መ/ ዓለም አቀፍ ማህበረሰብን ስንመለከት በአፓርታይድ ዘመን ዓለም ድምፁን ያሰማው ለምሳሌ ትልቁ ከሚባለው የሻርፕቪል እልቂት ላይ የሞተው የሰው ቁጥር 64 ሰው ነበር።በእዚህ ብዙ አገሮች ከደቡብ አፍሪካ ጋር ያላቸውን ግንኙነት እንዲያቆሙ ሆነዋል።እኛ ጋር በ1997 ዓም ብቻ እራሳቸው እንዳመኑት 197 ሰው ሲገደል ዓለም ለእኛ አይጮህም።ጋምቤላ ከ400 ሰው በላይ ሲያልቅ ዓለም አይናገረም። በቅርቡ በኦሮሞ ወንድሞቻችን ላይ ከ500 በላይ ሲገደሉ ከ30ሺህ በላይ እስር ቤት ስታጎሩ ዓለም እንዳልሰማ ዝም ብሏል። ካሉ በኃላ ፕሮፌሰር ብርሃኑ በመቀጠል እንዲህ አሉ:
”ስለሆነም አሁን ዓለም ተቀይሯል።ማንም ፈረንጅ ለእኛ ችግር ከእኛ በላይ ማንም መፍትሄ ሊያመጣ አይችልም።ነፃነት አጥተህ መብላት መጠጣትህ ሰው አያደርግህም።” ብለዋል።በመጨረሻም ስለ አርበኞች ግንቦት 7 መጪ የትግል ሂደት ሲያስረዱ ይህንን ብለዋል:
መጪው ትግላችን ትግሉን በድንበር አካባቢ ማቆየት ሳይሆን ወያኔ በር ድረስ ማድረስ ነው።እዚህም አብዛኛውን የወያኔ ኃይል ለትግሉ ማሰለፍ ነው።ይህ ትግል ወያኔዎችን እራሳቸውን አሳምኖ ለሕዝብ እንዲቆሙ ማድረግ መቻል አለበት። እናንተም ስታገኙዋቸው ደግግማችሁ ጥቂቶች ስለሚሰሩት አስረዷቸው። በነገራችን ላይ የኢትዮጵያ ሰራዊት ጋር እኛ ፀብ የለንም።የእኛ አላማ እንደ ወያኔ ተቋማትን ማፍረስ አይደለም። ያሉትን ጠብቀን የተሻሉ መገንባት ነው።እኛ ከድል በኃላ አሁን ያለውን ሰራዊት የምናፈርስበት ምንም ምክንያት የለም ብለዋል።

No comments:

Post a Comment