Thursday, February 11, 2016

እነ ሀብታሙ አያሌው ከእስር ሊፈቱ ነው ተባለ በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር




በፌደራል አቃቤ ህግ ይግባኝ ተጠይቆባቸው ጉዳያቸውን በእስር ቤት ሆነው እየተከታተሉ የሚገኙት የቀድሞው አንድነት፣ የሰማያዊ እና የአረና ፓርቲዎች አመራሮችና መምህር አብርሃም ሰለሞን ከእስር እንዲፈቱ ትዕዛዝ እንደሚጽፍ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ዛሬ አስታውቋል፡፡
በቃሊቲ ማረሚያ ቤት አስተዳደር በደል እየተፈጸመብን ነው በሚል አቶ የሺዋስ አሰፋ፣ አቶ አብርሃ ደስታ እና አቶ ዳንኤል ሺበሽ የካቲት 1/2008 ዓ.ም ባሰሙት አቤቱታ ላይ ማረሚያ ቤቱ መልስ እንዲሰጥ ለዛሬ የካቲት 3/2008 ዓ.ም ተቀጥሮ በነበረው መሰረት ችሎት የቀረቡት ሦስቱ ይግባኝ መልስ ሰጭዎች ከማረሚያ ቤቱ መልስ ሳይሆን ‹‹ነገ መፈቻችሁ ይጻፍላችኋል›› የሚል መልስ ከዳኛ ዳኜ መላኩ ተነግሯቸዋል፡፡
ይግባኝ መልስ ሰጭዎቹ አቶ ሀብታሙ አያሌው፣ አቶ የሺዋስ አሰፋ፣ አቶ አብርሃ ደስታ፣ አቶ ዳንኤል ሺበሽና መምህር አብርሃም ሰለሞን የስር ፍርድ ቤት ነሀሴ 14/2007 ዓ.ም በነጻ እንዲሰናበቱ መወሰኑን ተከትሎ ከእስር መፈታት ነበረባቸው የሚለውን ውሳኔ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት መወሰኑ የሚታወስ ሲሆን የአሁኑ የመፈታት ውሳኔም የዚሁ ውጤት መሆኑ ተመልክቷል፡፡
ዳኛ ዳኜ መላኩ ለአቶ የሺዋስ አሰፋ፣ አቶ አብርሃ ደስታ እና ለአቶ ዳንኤል ሺበሽ ‹‹ነገ ለአምስታችሁም መፈቻችሁን እንልካለን፤ ሰኞ የሚኖራችሁን ቀጠሮ ከቤት መጥታችሁ ትከታተላላችሁ›› ሲሉ ነግረዋቸዋል፡፡ አምስቱ ይግባኝ መልስ ሰጭዎች በስር ፍርድ ቤት ነጻ ከተባሉ ሰባት ወራት ተቆጥረዋል፡

No comments:

Post a Comment