Sunday, February 21, 2016

የቆሰለው አውሬ አገራችንን ይበልጥ ሳያቆስል በጊዜ እንነሳ! February 20, 2016


def-thumb
የንቅናቄያችን ሊቀመንበር ፕ/ር ብርሃኑ ነጋ በቅርቡ በዋሽንግተን ዲሲ ተገኝተው ለኢትዮጵያውያን ባደረጉት ንግግር ወያኔ የቆሰለ አውሬ ሆኗል ብለው ነበር። ፕ/ር ብርሃኑ በንግግራቸው፣ የቆሰለ አውሬ በህይወት ለመቆየት ሲል ያለ የሌለውን ሃይል በመጠቀም ጥቃት በሰነዘረበት ግለሰብ ላይ የበቀል እርምጃ ከመውሰድ ወደ ሁዋላ የማይል በመሆኑ፣ ጥቃቱን ለመከላከል በቂ ዝግጅት ማድረግ እንደሚገባ አሳስበው ነበር። አውሬነት የጭካኔ ደረጃንና ሁዋላቀርነትን የሚያሳይ ገላጭ ቃል ነው፤ አውሬነት ወያኔ በህዝባችን ላይ ለሚፈጽመው ግፍ ጥሩ ወካይ ቃል ነው፤ ነገር ግን ወያኔ ከአውሬ አልፎ የቆሰለ አውሬ ሆኗል፤ አደገኛነቱም ጨምሯል።

ፕ/ር ብርሃኑ በትክክል እንዳሉት የወያኔ የጥቃት ኢላማዎች ወያኔን የሚታገሉት የነጻነት ሃይሎች ብቻ አይሆኑም። መላው የአገራችን ህዝብ በቆሰለው አውሬ ከመጎዳት አያመልጥም። በነፍስ ግቢና ውጪ መካከል የሚገኘው የቆሰለው አውሬ አፈር ልሶ ከቁስለቱ አገግሞ እንዳይነሳ ጥፋቱን እየተከላከሉ፣ ሞቱ የሚፋጠንበትን መንገድ መቀየስ ከእያንዳንዱ ዜጋ ይጠበቃል። የቆሰለ አውሬ ወዳጅ ጠላት መለየት የማይችል፣ ፊት ለፊት ባገኘው ላይ ሁሉ እርምጃ ለመወሰድ የሚንደፋደፍ በመሆኑ፣ ሁሉም ዜጋ የጥቃት ጥፎሮቹ እሱም ላይ እንደሚያርፉ በመገንዘብ አውሬውን ለማጥፋት መረባረብ ይኖርበታል።

ሰሞኑን በኦሮሚያ አካባቢ እየተቀጣጠለ በመጣው ህዝባዊ እምቢተኝነት ወደ ከርሰ መቃብር እየተገፈተረ መሆኑ የገባውና የቆሰለ አውሬነት ባህሪውን በይፋ ማሳየት የጀመረው ይህ የወያኔ አገዛዝ አጥፍቶ ለመጥፋት አንዱን ሃይማኖት ከሌላው ሃይማኖት፡ አንዱን ብሄር ከሌላው ብሄር በማጋጨት የመፈራገጥ እርምጃውን ተያይዞታል:: ተጨማሪ ጊዜና እድል ከተሰጠውም ሌሎች ከዚህ የከፉ ድርጊቶችንም ሊፈጽም እንደሚችል ልብ ማለት ያሻል። ከዚህ ቀደም በተለያዩ አካባቢዎች በሰው ህይወትና በንብረት ላይ ጉዳት ሊያደርስ የሚችል ፍንዳታዎችን ሲያካሄድ የነበረ አገዛዝ ወደዚያ ልማዱ ተመልሶ ጉዳት ለማድረስ ወደኋላ የማይመለስ ብቻ ሳይሆን ተሰሚነት አላቸው የሚባሉትን ወይም ከሌላ ብሄረሰብ የሆኑትን በማስገደል በቀል ሊያስነሳ የሚችል ግጭት ሊቀሰቅስ እንደሚችል ይጠበቃል:: በኦሮምያና ተቃውሞ በሚያይልባቸው ሌሎች አካባቢዎች የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በማወጅ ህዝቡን በርሃብ ከመቅጣትም ወደ ኋላ የመለሳል ብሎ ለማሰብ ይከብዳል:: ማምሻም እድሜ ነው እንደሚባለው ወያኔ ህዝባችንን በማጋጨት እስትንፋሱን ለአንድ ቀን የሚያረዝም እስከመሰለው ድረስ የሚችለውን ሰይጣናዊ መንገዶች ሁሉ ከመሞከር የማይታቀብ ፍጡር መሆኑ ጥርጣሬ ውስጥ የሚገባ አይደለም:: ይህ ሁሉ ሙከራ ከከሸፈበትና እንደማያዋጣው ከተረዳ በዘረፋና በሙስና የሰበሰበውን ሃብትና ንብረት ማሸሹን አጠናክሮ ይገፋበታል።
አርበኞች ግንቦት7 በ11ኛው ሰአት የሚገኘውን የቆሰለውን አውሬ ጥፋት ለመቀነስም ሆነ ግብዓተ መሬቱን ለማፋጠን ፣ በወታደራዊው እና በህዝባዊ እምቢተኝነቱ መስኮች ተግቶ እየሰራ ነው። ንቅናቄው ሁኔታዎችን ሁሉ አጥንቶ ተስማሚ ሆኖ ባገኘበት ሰዓት በቆሰለው አውሬ ላይ የማያዳግም እርምጃ እንደሚወስድ ለኢትዮጵያ ህዝብ በተደጋጋሚ ገልጿል። ንቅናቄያችን አገራችንን ከቆሰለው አውሬ ቁጥጥር ሙሉ በሙሉ ካላቀቀ በሁዋላ፣ ሁሉም ኢትዮጵያዊ በጋራ መክሮና ዘክሮ የሚገነባት የነጻነትና የእኩልነት አገር እንዲኖረን ለማስቻል አቅም የፈቀደለትን ሁሉ ከማድረግ ለአፍታም ቢሆን ወደ ኋላ እንደማይል ፣ የንቅናቄው ሊቀመንበር እና የመላው አባላቱ ተወካዮች በቅርቡ ባካሄዱዋቸው ጉባኤዎች በድጋሜ አረጋግጠዋል።
በአገር ቤትና በውጪ የሚኖረው ህዝባችንም በበኩሉ ይህ የቆሰለ አውሬ የሚወስዳቸውን እርምጃዎች ለማክሸፍ ከዚህ የሚከተሉትን እርምጃዎች እንደአካባቢው ተጨባጭ ሁኔታ መውሰድ ይኖርበታል።
1ኛ. በየቀኑ የሚካሄዱ ህዝባዊ እንቅስቃሴዎችን ትኩረት ሰጥቶ መከታተልና መረጃ መሰብሰብ:: ያገኛቸውንም መረጃዎች ወዲያውኑ ለመገናኛ ብዙሃን ማቀበል
2ኛ. የቆሰለው አውሬ አንዱን ሃይማኖት ከሌላው ሃይማኖት፣ አንዱን ብሄር ከሌላው ብሄር ለማጋጨት የሚያደርገውን ጥረት ማክሸፍንና ፣ ማጋለጥ።
3ኛ. ለዚህ እኩይ ስራ የሚሰለፉ ሃይሎችን ማስጠንቀቅ፣ ማጋለጥና እንደ አስፈላጊነቱ ተመጣጣኝ እርምጃ መውሰድ።
4ኛ. በየአካባቢው የተቀሰቀሱ ተቃውሞዎችን ትንሽ ትልቅ ሳይባል መቀላቀል። በተለይ የወያኔ የነርቭ ማእከል ናቸው በሚባሉት ተቋማት ላይ እርምጃ መውሰድ።
5ኛ. የወያኔን አገዛዝ ለመለወጥ በትግል ላይ ያሉ ድርጅቶችን በማቴሪያል፣ በገንዘብና በማንኛውም ነገር መርዳት።
6ኛ. በሁለገብ ትግሉ እየተሳተፉ ያሉ ሃይሎችን በአካል መቀላቀል፣ ካልተቻለም መረጃ በማቀበል ማገዝ።
7ኛ. ወያኔ በመካከላችን የዘረጋውን የልዩነት አጥር በማፍረስ ጥርጣሬና አለመተማመን እንዳይኖር ማድረግ፡ እያንዳንዱ ለሁሉም ሁሉም ለያንዳንዱ ወገናዊነቱን መግለጽ፤ የጎንዮሽ ሽኩቻዎችን ማቆምና የፖለቲካ መስመር ልዩነቶቻችንን ለማጥበብ ዝግጁ መሆን።
8ኛ. የእርስ በርስ ትብብርን ማጠናከር አንዱ ሲጎዳ ሌላው እያከመ፣ ሁሉም ተቃውሞውን በየአቅጣጫው መጀመር።
አርበኞች ግንቦት7 እንደቆሰለ አውሬ መፈራገጥ የጀመረው የወያኔ አገዛዝ በአገራችንና በህዝባችን ላይ ሊያደርስ የሚችለው አደጋ እንዲቀንስና ድህሬ ወያኔ የህዝቦቿን አንድነት በእኩልነት የምታረጋግጥ የተረጋጋች ፣ ሰላምና ብልጽግና የሰፈነባት አገር ለመመሥረት ከሚሹ የአገሪቱ ልጆች ሁሉ ጋር እጅ ለእጅ በመያያዝ የነጻነት ቀን እንደሚያቃርብ እርግጠኛ ነው ።
የወያኔን የሥልጣን እድሜ ለማሳጠር ሁላችንም ለተግባራዊ ትግል ዛሬውኑ ታጥቀን በቆራጥነት እንነሳ!
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ !
አርበኞች ግንቦት7

No comments:

Post a Comment