Wednesday, October 12, 2016

አንጌላ መርከል መንግስት በሰላማዊ መንገድ ጥያቄን በሚያቅርቡ ሰዎች ላይ የሚወሰደውን ዕርምጃ እንዲያቆም አሳሰቡ ኢሳት (ጥቅምት 1 ፥ 2008)


በኢትዮጵያ ጉብኝት እያደረጉ ያሉት የጀርመኗ ቻንስለር አንጌላ መርከል መንግስት በሰላማዊ መንገድ ጥያቄን በሚያቅርቡ አካላት ላይ የሚወሰደውን ዕርምጃ እንዲያቆም ማከሰኞ አሳሰቡ።
ከጠቅላይ ሚኒስትር አቶ ሃይለማሪያም ደሳለኝ ጋ በመሆን የጋራ መግለጫን የሰጡት መርከል “ችግር/ጥያቄ ካላቸው ሰዎች ጋር መወያየት ይኖርባችኋል” ሲሉ ለአቶ ሃይለማሪያም በመግለጫው ስነስርዓት ወቅት መናገራቸው ሮይተርስ ዘግቧል።
የመንግስት የጸጥታ ሃይሎች በሰላማዊ ሰልፈኞች ላይ የሚወስዱትን ድርጊት የኮነኑት የጀርመኗ ቻንስለር በስልጣን ላይ ያለውን ገዢው የኢህአዴግ መንግስት የፖለቲካ ምህዳሩን ክፍት እንዲያደርግም ጠይቀዋል።

ሃገሪቱ በአስቸኳይ የጊዜ አዋጅ ውስጥ እያለች ጉብኝታቸውን እያደረጉ ያሉት አንጌላ መርከል በዲሞክራሲ ሂደት ውስጥ ድምፅን የሚያሰሙ የተቃዋሚ አካላት በፓርላማ ውስጥ ተሳታፊ መሆናቸው እጅግ አስፈላጊ መሆኑንም ለመገናኛ ብዙሃን አስረድተዋል።
የጀርመኗ ቻንስለር በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ተገኘተው ንግግር እንዲያደርጉ በኢትዮጵያ መንግስት ጥያቄ ቢቀርብላቸውም አንገላ መርከል የተቃዋሚ ፓርቲ ተወካይ በሌለበት ፓርላማ ንግግሩን ለማድረግ ፈቃደኛ ሳይሆኑ መቅረታቸውን ስማቸውን መግለጽ ያልፈለጉ ዲፕሎማቶች ለሮይተርስ ተናግረዋል።
“በቻንስለሯ በኩል የተሰጠው ምላሽ ጀርመን የተለመደውን አካሄድ እየተከተለች እንዳለሆነ ማሳያ “ ሲሉ እነዚሁ ዲፕሎማት አከለው አስረድተዋል።
በኢትዮጵያ ባለው ወቅታዊ የፖለቲካ ትኩሳት ስጋት እንዳደረባቸው የሚናገሩት መርከል በነጻነት የሚንቀሳቀሱ የሲቪል ማህበረሰብ ከአንድ ሃገር የዴሞክራሲ ግንባታ ወሳኝ መሆኑንም በአጽንዖት ገልጸዋል።
ቻንስለሯ ያላቸውን ስጋት ማቅረባቸውን ተከትሎ ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማሪያም ደሳለኝ መንግስታቸው የፖለቲካ ምህዳሩን ለማስፋት ጥረት እያደረገ ነው ሲሉ ምላሽ ሰጥተዋል።
በኢትዮጵያ በተለያዩ የኢንቨስትመንት ስራ ውስጥ ተሰማርተው የሚገኙ የጀርመን ባለሃብቶች ቅሬታን እያቀረቡ ይፋ ያደረጉት መርከል መንግስት ባለሃብቶቹ ላቀረቡት ቅሬታ በጎ ምላሽን እንዲሰጥ መጠየቃቸውም ታውቋል።
ባለፈው ሳምንት አንድ የእስራዔል የማዕድን ኩባንያ መንግስት የገባውን ቃል ተግባራዊ አላደረገም በማለት ከአፋር ክልል ከተሰማራበት የፖታሽ ማዕድን ስራ ጠቅልሎ መወጣቱን ይፋ ማድረጉ ይታወሳል።
በማዕከላዊ ሶማሊያ ቁልፍ ወታደራዊ ስፍራዎችን ይዘው የቆዩት የኢትዮጵያ ወታደሮች የተቃጣባቸውን ጥቃት ተከትሎ አካባቢውን ለቀው ወጡ።
ወታደሮቹ ስፍራውን በለቀቁ በሰዓታት ልዩነት ውስጥ ጥቃቱን አድርሷል የተባለው የሶማሊያ ታጣቂ ሃይል አልሸባብ አካባቢውን እንደተቆጣጠረው ቢቢሲ የተለያዩ መረጃዎችን ዋቢ ብማድረግ ሰውኞ ዘግቧል።

No comments:

Post a Comment