Friday, December 4, 2015

ብአዴንን ህዝባዊ ወገንተኝነት ያያችህ? (ከጠረፈኛው የፍትህ ርሃብተኛ፤ ቂልንጦ ማጎሪያ ቤት)


ህዝባዊ ነኝ ብሎ የሚያወራ ወይም የሚመኝ ሁሉ ህዝባዊ ሊሆን አይችልም፡፡ በተግባር መሬት ላይ ላለው ህዝብ ጠብ የሚል ህዝባዊነትን የሚሸት ተግባራትን ካልፈፀመ፡፡ በእኔ እይታ የብአዴንን ህዝባዊነትና አድርባይነቱን፣ አፋዊና ተግባራዊነቱን መዝኜ ስመለከተው ህዝባዊነቱና ተግባራዊነቱ ቀልሎ ተገኝቷል፡፡ በመሆኑም ብአዴን አድርባይ አፋዊ እና ጥገኛ ፓርቲ እንጂ የራሱን ማንነት ጠብቆ ህዝባዊነቱን ያስቀጠለ ድርጅት አይደለም፡፡ በብአዴን እየተሠራ ያለው ሆድ አደርነት፣ አድርባይነት፣ ግላዊነት፣ የግለሰብ ኪስ አድላቢነትና ማን አለብኝነትን እንጂ በማንኛውም መልኩ ካመጣቸው ለውጦች ይልቅ ያጠፋቸው ታሪካዊ ስህተቶች እና ውድቀቶች ለውጥ የሚለውን ቃል አፈርድሜ አብልተውታል፡፡ 
ህዝባዊነት ሲባል ለህዝብ ሲሉ እንደ ሻማ ቀልጠው ብርሃን መስጠትን፣ ለህዝብ ሲሉ የግል ጥቅም ማጣትን /መተውን/፣ ለህዝብ ተገቢውን መስዋዕትነት መክፈልን፣ ኃላፊነትን በአግባቡ መውጣትን፣ የህዝብ ሀብትና ንብትን በአግባቡ መጠበቅና መንከባከብን፣ ለህዝብ ጥያቄ ምላሽ መስጠትን አካባቢውን ወደ ተሻለ የዕድገት ጎዳና መለወጥን፣ በኢኮኖሚያዊ በማህበራዊና በፖለቲካዊ ጉዳዮች ላይ ተራማጅ አስተሳሰቦችን ማምጣትን ይጠይቃል፡፡ በሀሳብና በህግ የበላይነት ማመንን፣ ስለ እውነትና ታሪክ ወግና ባህል መከበር ዘብ መቆምን፣ ድህነትን ድንቁርናና ጦርነትን በማስወገድ የሠላምና የፀጥታ የሠብአዊነት የዲሞክራሲያዊ መብት፣ የእኩልነት የፍትህ፣ የመልካም አስተዳደርና የፈጣንና ቀልጣፋ አገልግሎት ተጠቃሚዎች በማድረግ፤ ከህዝብ ፊት ሆኖ መሠናክሎችን በአሳታፊነት፣ በመቻቻልና በውይይት በመፍታት ዋጋ መክፈልን ይጠይቃል፡፡ ህዝባዊነት!
ህዝባዊነት አስፈላጊ ብቻ መሆን አይችልም! መፈለግ አንዱ ቅድመ ሁኔታ ቢሆንም ዋነኛው ነገር በተግባር ማሳየት ነው፡፡ ስለዚህ በቅድሚያ ራስን ማሸነፍ ይጠይቃል፤ ከራስ ጋር መታረቅን ይጠይቃል፡፡ እንዲሁም መቅደም ያለበትን ለይቶ ማስቀደምንና መከተል ያለበትን ማስከተልን ይጠይቃል፡፡
ህዝባዊነት ርዕስ አድርጌ የወሰድኩበት ዋነኛ ምክንያት ኢህዴን - ብአዴን ከሠሞኑ 35ኛ ዓመት የምስረታ በዓሉን በከፍተኛ ድግስ በመላ ሀገሪቱ በሚገኙ የተመረጡ ቦታዎችና እስከ ጎረቤት ሀገር ጅቡቲም ድረስ በመሄድ “እወቁልኝ፣ የመናገር መብቴ በ35 ዓመት በወያኔ ተፈቀደልኝ፣ ብሉ ጠጡልኝ፣ ድሌ ዛሬ ነው፣ ሠርጌ ዛሬ ነው ይህ የመጨረሻዬ ነው” በሚመስል መልኩ እያከበረ መሆኑ ነው፡፡ ዋናው መፈክሩም ‹‹የብአዴን ህዝባዊነት›› ላይ ያተኮረ በመሆኑ ጭምር ነው ርዕሴ ያደረኩት፡፡ የዘንድሮው በዓል ብአዴን ‹‹ለሠርጌ ያልሆነ ቀሚስ ይበጣጠስ›› በሚል ከወያኔ ነፃ የወጣ ይመስል፤ ለዚህ ለማይደገመው ሠርጌ ያልሆነ ገንዘብ ለምን ሊሆነኝ ነው በማለት በሩጫ፣ በኳስ ጨዋታ፣ በእስክስታ፣ በስነ-ፁሁፍ በ‹‹መስክ ጉብኝነት››፣ በ‹‹ፓናል ውይይት››፣ በጥያቄና መልስ፣ በውዝዋዜው፣ በከፍተኛ ወጭ ሽልማትና የመጠጥ የምግብ ዝግጅት ‹‹ታጥቄ እንደታገልኩት ታጥቄ እጠጣለሁ እጨፍራለሁ፣ በውስኪና በሻምፓኝ እረጫለሁ›› ሲል ተመልክተናል፡፡
ታጥቄ እስክስታ እመታለሁ፤ ሠልፍ እወጣለሁ፣ ሁሉንም የቴሌቭዥን ጣቢያዎች እቆጣጠራለሁ፣ በሺዎች የሚቆጠሩ ቲሸርቶችን፣ ፓንፕሌቶችን፣ ጋዜጦችን፣ መፅሄቶችንና መፅሀፍቶችን አሳትሜ እየቸበቸብኩ ነው ብሎናል፡፡ ይሄን ነው እንግዲህ ለብአዴን ህዝባዊነት ማለት፡፡ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎች በረሃብ አለንጋ እየተገረፉ ባሉበት፣ ህፃናት እየሞቱ በሚገኙበት፣ የነገ ሀገር ተረካቢ ወጣቶች በስደት ላይ ኩላሊታቸውን እየተነጠቁ የባህር አሳዎችና አዞዎች እጣፈንታ እየሆኑ፣ የመኪና አደጋ ሠለባዎች፣ የበርሃ ሲሳዮችና አንገታቸውን እንደ በግ እየታረዱ ባለት አሳዛኝና አሠቃቂ ጊዜ ላይ ይህ ሁሉ ድግስ ህዝባዊነትን ያሳይል? በቁስለኛው ህዝብ ላይ ተጨማሪ ቁስል ማፍራት ሀገር ቀምቶ በማሣደድ፣ ማሣረድ በሀሳብ ልዩነት የተነሣ በየ እስርቤቱ አሸባሪ የሚል ታርጋ በመለጠፍ እያጎሩ ማሰቃየት፣ ማኮላሸት በአካል በሞራሉ በስነ-ልቦናው ጫና መፍጠር ህዝባዊነት ነው ፀረ ህዝብነት?
ከሥራ እያፈናቀሉ፣ የሀሰት/የፈጠራ ወንጀልን እየፈጠሩ፣ በሀሰት አስገድደው እያስመሰከሩ፣ ወጣቱን በአካልና በአዕምኖ እየቀጠቀጡ ማደንዘዝ፣ ያለፍትህ ማጎር ነው የብአዴን ህዝባዊነት የሚባው የተቃርኖ ዓለም፡፡ በእርግጥ የቀጥተኛ አለቃው ወያኔ የተቃርኖ ዓለምም ተመሳሳይ ነው፡፡ በጣም የሚገርመው የአማራን ህዝብና ኦርቶዶክስን ፈርጀው ‹‹አከርካሪውን እንሰብራለን›› ብለው በጫካ ዕቅድ የተነሱት እነ ጄነራል ሳሞራ የኑስ እና አባይ ፀሃዬ ስለ ህዝብ አስተያየት መጠመዳቸው ነው፡፡ ምን የተፈጠረ አዲስ ነገር አለ?
ይህ ብአዴን ነው በሀገራችን ከ15 ሚሊዮን ህዝብ በላይ በድርቅና በረሃብ ላይ ባለበት ሁኔታ የ35 ዓመት የአሮጊት (ጋለሞታ) ድሮ ውስኪና ሻምፓኝ የሚራጨው፡፡ ሀገሪቱ አላዋቂ ሰዎች ሞልተውባታል፡፡ ብአዴንም ሆነ መሰል ድርጅቶች በአጉል ድንቁርና፣ ትዕቢትና እብሪት ተወጥረው በአስተሳሰብ ድህነት /ደዌ/ ተይዘው ወደፊት መንቀሳቀስ አቅቷቸው፣ መቆም ተስኗቸው ወደ ኋላ በማፈግፈግ ላይ ናቸው፡፡ 
ደም የገበሩትን አባቶቻችንና እናቶቻችንን ጠንቅቀን እናውቃለን፡፡ ግን የምንፈልገው አላማቸውን አስቀጥሎ የኢትዮጵያንና ክልሉን ህዝብ ከድህነት አረንቋ የሚያላቅቅ መሬት ላራሹ ጥያቄን የሚመልስ፣ ፍትህና እኩልነት የሚያሰፍን ነፃነትና ክብርን ሀገርን የማይቀማ፣ መንደርተኛ ያልሆነ፣ ኢትዮጵዊነት ያሠፈረ ድርጅትና አመራር ነበር፡፡ ግን አለመታደል ሆኖ በተቃራኒው ሆነ! ስለመበታተን የሚሰብክ፣ እወክለዋለሁ የሚለውን ህዝብ የሚያስጨፈጭፍ ሆነ! ብአዴን የህዝብ ወኪል ነኝ እያለ ከጥቃት ህዝብን ከመታደግ ይልቅ አላዳንኩሽምን ይዘምራል! የስቃይ ድምፅ እየቀረፀ ያዳምጣል፡፡ 
በአማራ ክልል ብዙ አሣፋሪና አሳዛኝ ድርጊቶችን እየተሰሩ ነው፡፡ ምሳሌዎችን እንመልከት፡- 
በክልሉ ውስጥ ሰዎች በአልሞ ተኳሽ ወታደሮች ተገድለው በመኪና ሲጉተቱ፣ ፀጉራቸው ከእንጨት ጋር ታስሮ በአስፓልት ላይ በህዝብ ፊት ሲጎተቱ አይተናል! አይቀበሩም (በቤተክርስቲያን ስርዓት) ተብሏል፤ ቤተሰብ እንዳያለቅስ የተከለከለ መሆኑን አይተናል (ምሳሌ በታች አርማጭዎ ሳንጃ ከተማ - እነ ሽንኩ ካፌና ዳኛው ይህ አረመኔያዊ ድርጊት ተፈፅሟል) ታዲያ ይህ ህዝባዊነት ወይስ ፀረ-ሕዝባዊነት?)
ሰዎችን ከእስር ቤት አስወጥተው ሲገድሉ አይተናል:: በፍ/ቤት ተከሰው ከ4 በላይ ሰዎች የምስክርነት ቃላቸውን ቢሰጡም ገዳዩ በሙስና በነፃ ተለቋል፡፡ (ታች አርማጭ ወረዳ ወጣት ጎሹ እያዩ ሲገደል፡፡) በሀሳብ ልዩነት መጠፋፋት የለብንም ይላል የብአዴን መፈክር፡፡ ግን ብአዴን በመቃወማችንና ባለመደገፋቸው የተነሳ የመኖር መብታቸው ተገፎ (ጭቆና ግፍና በደል) በዝቶባቸው ኑሯቸውን፣ የሞቀ ቤታቸውን፣ ሚስታቸውንና ልጃቸውን ትተው ኑሯቸውን ጫካ ያደረጉ ወገኖች እንዳሉ ታዝበናል! የሽፍታ ቤተሰብ /ወገን/ በመሆናቸው ብቻ ‹‹ገደላችህ አስክሬን አምጡ!›› እየተባሉ ልጆቻቸው ለመግደል ፈቃደኛ ባመሆናቸው የተነሳ መሬታቸውን የተነጠቁ፣ እርሻ ቦታቸውን ወደ ከተማ እንዲገቡ የተገደዱ በኑሮ ውድነትና በእስር እየተሰቃዩ ያሉ ሰዎችን አየን፡፡
የህግ የበላይነት ተጥሶ የግለሰብ የበላይነት ሰፍኖ በቂም በቀልና በስነ-ልቦና ሰዎች ተሰቃይተዋል፡፡ የዘር ማጥፋት ድርጊት የተፈፀመባቸውን የወልቃት አርማጭሆ ነዋሪዎችን አይተናል፡፡ በብሎክ የህዝብ መሬትን በመሸንሸን ለሀገር ውስጥና ለውጭ ጥቅመኛ ባለሀብቶች ሲሸጡ አይተናል፡፡ የመኖገር፣ የማሰብ፣ ያለመሰቃየት መብት አላችሁ እየተባለ በተቃራኒው ግለሰቦች በጉባኤ በመናገራቸው በጅምላና በጭፍን ፍርጃ ፀረ-ሠላም፣ ፀረ-ዴሞክራሲ፣ አሸባሪ እያሉ በማሰባቸውም እየታሰሩ ነው፡፡ ሀሰት ነግሶ፣ እውነት ተገርስሶ፣ በውሸት ሪፖርት፣ በፈጠራ ክስ ኑሮአቸውን ያደረጉ ወገኖችን አይተናል፡፡ 
ብአዴን ጥገኛ ሲሆን ወያኔ በበላይነት አገሪቱንም ድርጅቶች ሲያስከብር ኖሯል፡፡ ዛሬ ብአዴን በ35 ኣመቷ ዳሩኝ ማለቷ የሀገራችን ባህል ወይም ስርኣትን የጣሰ ነው፡፡ ‹‹የጋለሞታ/ የአሮጌቶች›› ጋብቻ ነው! ስካሁን ድረስ ወያኔ ባሪያ አድርጓት ከቆየ በኋላ ትንፍሽ ብላ የማታውቀ ለመጨፈር አስፈቅዳለች፤ ጎጠኝነት አስተምሯት ቅማንት አማራና አገው ብቻ ሳይሆን በጎጥ እየተከፋፈለ የቀን ሠራኛው ሲገደል አይተናል፡፡ የክልሉ ዜጎች ሲፈናቀሉ ምላሽ መስጠት ሲሳናት አይተናል፡፡ የኮንትሮባንድ ንግድ በመኪና እየነገደች ቲሸርትና ኦሞ የያዘን ድሃ ትወርሳለች፡፡ ታዲያ የብአዴን ዲሞክራሲያዊነትና ህዝባዊነት የት ላይ ነው?

No comments:

Post a Comment