Thursday, December 8, 2016

ኢትዮጵያ በኢንተርኔት አገልግሎት ላይ የከፋ አፈናን ከሚፈጽሙ ሃገራት መካከል ግንባር ቀደም ሃገር ተብላ ተፈረጀች ኢሳት (ኅዳር 29 ፥ 2009)


ኢትዮጵያ በተያዘው 2016 የፈረንጆች አም በኢንተርኔት አገልግሎት ላይ የከፋ አፈናን ከሚፈጽሙ ሃገራት መካከል ግንባር ቀደም ሃገር ተብላ ተፈረጀች።
በቴክኖሎጂው አጠቃቀምና ተደራሽነት እንዲሁም ቁጥጥር ዙሪያ አመታዊ ጥናቱን ይፋ ያደረገው ፍሪደም ሃውስ የተሰኘ ተቋም ቻይና፣ ሶሪያና ኢትዮጵያ የከፋ የተባለ አፈናን ከሚፈጽሙ ሃገራት መካከል ዋነኛ መሆናቸውን ይፋ አድርጓል።
ካለፈው አመት ጀምሮ ኢንተርኔት አገልግሎት ላይ እገዳንና ቁጥጥርን ተግባራዊ አድርጋ የምትገኘው ኢትዮጵያ በአፍሪካ ከሚገኙ 54 ሃገራት መካከል የቴክኖሎጂው ጠላት ተደርጋ ተፈርጃለች።
በኦሮሚያ ክልል የተቀሰቀሰውን ህዝባዊ ተቃውሞ የኢትዮጵያ መንግስት በመደበኛውና በተጓዳኝ የኢንተርኔት አገልግሎት ላይ እገዳን ጥሎ የሚገኝ ሲሆን፣ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መውጣቱን ምክንያት በማድረግም አገልግሎቱ ታግዶ ይገኛል።
ለአምስት አመት ያህል በእርስ በርስ ጦርነት ውስጥ ካለችው ሶሪያ ተርታ የተመደበችው ኢትዮጵያ፣ የኢንተርኔት አገልግሎትን ከመቆጣጠርና ከማገድ በተጨማሪ የተጠቃሚዎችን መብት በመግፈፍ ወደር የሌላት ሃገር ተደርጋ በሰብዓዊ መብት ተሟጋች ድርጅቱ ሪፖርት ተቀምጣለች።
የማህበራዊ ድረ-ገጾችም በመጠቀም የግል አስተያየታቸውን ያሰፈሩት በርካታ ግለሰቦች እንዲሁም ጋዜጠኞችና የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ግለሰቦች በመንግስት ለእስር መብቃታቸውም ተመልክቷል።
እንደፈረንጆቹ አቆጣጠር በ2015 ዓም ከነበራት ደረጃ ከዜሮ በታች በሆነ ቁጥር ማሽቆልቆልን ያስመዘገበችው ኢትዮጵያ፣ አገልግሎቱን ይበልጥ ለመቆጣጠር ይረዳት ዘንድ አቅርቡ በቴክኖሎጂው አጠቃቀም ዙሪያ ጠንካራ አዋጅ ተግባራዊ ማድረጓን ፍሪደም ሃውስ አመልክቷል።
ደቡብ አፍሪካ፣ አንጎላ፣ ዚምባብዌ፣ዛምቢያ፣ ማላዊ እና ሞሮኮ በኢንተርኔት ነጻነት ከአፍሪካ የተሻሉ ሃገራት ተብለ የተቀመጡ ሲሆን፣ ከ90 ሚሊዮን በላይ ህዝብ ያላት ኢትዮጵያ በቴክኖሎጂው ተጠቃሚዎች ላይ አስከፊ ቁጥጥር ተግባራዊ ማድረጓ ታውቋል።
አይስላንድ፣ ካናዳ፣ አውስትራሊያ፣ ጀርመን፣ ኢስቶኒያ፣ አሜሪካ፣ ጣሊያን እንዲሁም ብሪታኒያ ለዜጎቻቸው አገልግሎት በነጻነት ከሚያቀርቡ ግንባት ቀደም ሃገራት ተርታ ተፈርጀዋል።
35 በመቶ የሚሆነው የአለም ህዝብ የኢንተርኔት አገልግሎት በነጻነት የሚያገኝ ተደርጎ የተፈረጀ ሲሆን፣ 29 በመቶ የሚሆነው በከፊል እንዲሁም 24 በመቶ ብቻ በነጻነት ተጠቃሚ መሆኑን ከሪፖርቱ ለመረዳት ተችሏል።
በኢትዮጵያ በኢንተርኔት አገልግሎት ላይ የተጣለውን እገዳ ተከትሎ መቀመጫቸውን በአዲስ አበባ ያደረጉ የተለያዩ ሃገራትና አለም አቀፍ ተቋማት የእለት ከእለት ስራቸውን ማከናወን እንዳልቻሉ ሲገልጹ ቆይተዋል።
በጉዳዩ ዙሪያ ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ባለስልጣናት ጋር ተከታታይ ምክክርን ያደረጉ እነዚሁ አካላት እገዳው መቼ እንደሚያበቃ ጥያቄን ቢያቀርቡም ምላሽ ሳይሰጣቸው ሰንብቷል።

No comments:

Post a Comment