Monday, December 5, 2016

በሰሜን ጎንደር ዞን የሚንቀሳቀሱ የነጻነት ሃይሎች ከህወሃት/ኢህአዴግ ጦር ጋር እያደረጉ ባለው ጦርነት ድል እየቀናቸው መሆኑን ለኢሳት ተናግረዋል።ኅዳር ፳፮ (ሃያ ስድስት)ቀን ፳፻፱ ዓ/ም ኢሳት ዜና :-



Bilderesultat for የነጻነት ሃይሎችበውጊያው በመሳተፍ ላይ ካሉት መካከል አንዱ በሰሞኑ ወጊያ መትረጊስ ሳይቀር መማረኩን እና በርካታ ወታደሮች መገደላቸውን ገልጿል። ወኪላችን የሰሞኑን የውጊያ ውሎ በማስመለከት በላከው ሪፖርት አገዛዙ የበቀል እርምጃ ለመውሰድ እየተንቀሳቀሰ ነው። በዳባት ወረዳ በአጅሬ ጃኖራ ከህዳር 22 እስከ ህዳር 25 ድረስ የአገዛዙ ጦር በታጋዮቹ ላይ ድንገተኛ ጥቃት ለመፈጸም በተንቀሳቀሰበት ወቀት፣ 29 ወታደሮች ሲገደሉ ከ15 በላይ ቆስለዋል ፤ የተማረኩ ወታደሮችም አሉ፡፡ በጦርነቱ የተገደሉ የ 15 ወታደሮች አስከሬን በበራ ወንዝ ማዶ ወድቆ አልተነሳም። ቀዝቃዚት ተብሎ በሚጠራው ቦታ በተደረገው ውጊያ ወደ አካባቢው የተንቀሳቀሰው የአገዛዙ ጦር ሙሉ በሙሉ መደምሰሱን ወኪላችን ገልጿል። ውጊያውን የመሩት 2ቱ አንዱ የበየዳ ሌላው የወሎ ተወላጅ የመቶ አለቅነት ማእረግ ያላቸው የአገዛዙ ታማኝ ወታደሮች የተገደሉ ሲሆን፣ ወታደሮችን ከፊት ሆኖ እየመራ ወደ ታጋዮቹ ለመውሰድ የሞከረው ሚሊሺያ ምስጋናው አለሙ ክፉኛ ቆስሎ በህክምና ላይ ነው። ቁስለኞች በአምባጊዮርጊስእና በጎንደር ሆስፒታል በህክምና ላይ ይገኛሉ። በወገራ ወረዳ እንቃሽ አካባቢ ከህዳር 24 እስከ 25 በተደረገው ውጊያ ደግሞ ከጸረ ሽብር ግብረሃይል አባላት መካከል 4፣ ከሚሊሺያ ደግሞ 3 መገደላቸውን ፣ ሁለት የመትረጊስ ተኳሽ አባላት ይዘውት የነበረውን መትረየስ ለነጻነት ታጋዮች ማስረከባቸውን እንዲሁም 7 የአገዛዙ ወታደሮች ትግሉን መቀላቀላቸውን ወኪላችን ገልጿል። በእስካሁኑ ውጊያ ከ16 በላይ የነብስ ወከፍ መሳሪያዎች፣ 3 መትረየስ፣ ከቡድን መሳሪያ ደግሞ 7 ስናይፐር የጦር መሳሪያዎች ተማርከዋል ። በዚሁ አካባቢ የሚካሄደው ውጊያ አሁንም ድረስ የቀጠለ ሲሆን ፣ አገዛዙ ሃይሉን ወደ አካባቢው እያስጠጋ ነው። በሰሞኑ ጦርነት ከተሰታፉት መካከል አንድ የነጻነት ሃይል ያገኙትን ድል በዝርዝር ገልጸዋል። ታጋዮቹ “ የህወሃት መሪዎች እርስ በርስ እንድንጫረስ ለማድረግ እየሞከሩ በመሆኑ ፣ ወታደሮቹ ቆም ብለው እንዲያስቡ” በድጋሜ ጥሪ አቅርበዋል። ህዝቡ እስካሁን ላሳየው ድጋፍም ምስጋናቸውን ገልጸዋል። ድጋፉ በዚህ ከቀጠለ አካባቢውን ነጻ እንደሚያወጡትም ተናግረዋል። በአካባቢው ህዝብ ድርጊት የተበሳጨ የሚመስለው አገዛዙ፣ በበቀል በመነሳሳት የእህል ክምር እንዲሁም የ11 አርሶአደሮችን ቤት አቃጥሎአል። ቤታቸው ከተቃጠለባቸው ሰዎች መካከል ተሸመ ደሴ ፣ መለሰ ተሾመ፣ ታደለ መልሰው ፣ ደሞዝ ነጋሽ፣ ዘሬ ተዘራ ፣ ንጉስ ዘሬ፣ ለካው ይለፍ ፣ ደጉ ባዜ፣ ያለው አበበ ፣ ገብሬ ትዛዙ እና ምስጋናው አጣኔ ይገኙበታል። በሌላ ዜና ደግሞ በቋራ መንግስት ገበሬውን ትጥቅ ማስፈታት ጀምሯል ፡፡ በቋራ ወረዳ በ28 ኦራል መኪኖች የተጫኑ ወታደሮች ሻሽጌ ሰርከን በተባለው ቦታ በመስፈር በአካባቢው አርሶአደሮች ላይ ድብደባ በመፈጸም ትጥቅ እያስፈቱ ነው። አምባየ ገብሬ ፣ መኳንንት አለነ ፣ ደርብ ደማስ እና እንዳለው አቢታ የተባሉት አርሶአደሮች ትጥቃቸውን በሃይል እንዲፈቱ ተደርጓል። አርሶአደሮች ድብደባውን በመሸሽ የነጻነት ሃይሎችን እየተቀላቀሉ መሆኑንም ወኪላችን ከላከው ሪፖርት ለመረዳት ተችሎአል። በሰሜን ጎንደር ሰሞኑን ስለተካሄደው ጦርነት የህወሃት /ኢህአዴግ አገዛዝ የሰጠው መግለጫ የለም።

No comments:

Post a Comment