Wednesday, March 16, 2016

በአዲስ አበባ የሚገኙ የተለያዩ አካባቢዎች በወያኔ ጦር ቁጥጥር ስር ወደቁ ወያኔ በኮንሶ ሕዝብ ላይ ወታደራዊ ሽብር እያካሄደ ነው

  • በአዲስ አበባ የሚገኙ የተለያዩ  አካባቢዎች በወያኔ ጦር ቁጥጥር ስር ወደቁ
  • ወያኔ በኮንሶ ሕዝብ ላይ ወታደራዊ ሽብር እያካሄደ ነው
  • በናዝሬት የአዳማ ዩኒቨርስቲ አመጽ እንደገና ተቀሰቀሰ፤ የወያኔ አግአዚ ጦር ተማሪዎችን ደበደበ፤ አሰረ
  • በአዋሳ ዩኒቨርስቲም የወያኔ ጦር አፈሳና የጅምላ እስራት አካሄደ
  • የናይጀር ተቃዋሚ መሪ ከእስር እንዲፈቱ የተየቀውን ፍርድ ቤት ውድቅ አደረገው
  • በሞሮኮ የተደረገው የተቃውሞ ሰልፍ ባንኪ ሙንን አስቆጣ
  • ማይንማር (በርማ) አዲስ ፕሬዚዳንት አገኘች

የፍኖተ ዴሞክራሲ ራድዮ አጫጭር ዜናዎች

Ø ዛሬ መጋቢት 6 ቀን 2008 ዓም በአዲስ አበባ ያሉ የተለያዩ አካባቢዎች በወያኔ ልዩ የፌዴራል ጥበቃ ስር መወደቃቸው ታወቀ። የአዲስ አበባ ከተማ ይህ ዓይነት ጥበቃ የውጭ እንግዶች ሲመጡ ወይንም ወያኔ የራሱን በዓል ሲያከብር ብቻ እንደነበረ የሚናገሩ የዓይን እማኞች የዛሬው ልዩ ጥበቃ በምን ምክንያት እና ለምን ተግባር እንደሆነ የተናገረ ነገር ባይኖርም በተለይ አራት ኪሎ፤ አጼ ሚኒሊክ ቤተ መንግስት አካባቢው ጭምር በአግአዚ ጦር እየተጠበቀ ሲሆን አራት ኪሎ፤ ስድስት ኪሎ፤ አዋሬ፤ ካዛንችስ፤ ቀበና ፤ ሾላ ፒያሳ ከፍተኛ ቁጥር ያለው የወያኔ ፌዴራል ፖሊስ ልዩ ኃይል ተሰማርተው እንደነበር ታይተዋል። የወያኔ ቡድን መሪዎች በመላው ኢትዮጵያ የተቀጣጠለባቸው ሕዝባዊ ተቃውሞና ቁጣ የራሳቸው ጥላ እስኪያስበረግጋቸው ድረስ እያሰጋቸው ሲሆን ይህ ስጋትና ፍርሃታቸው ወደ ሕዝብ ለመመለስ ገዳይ ጦራቸውን በከተሞች ውስጥ በተለይም በአዲስ አበባ ከተማ በማሰማራት አስፈራርቶና አሸብሮ ለመሰንበት የሚጠቀሙበት ዘዴ እንደሆነ ይታወቃል። 
File Photo
File Photo

Ø የወያኔ ቡድን መሪዎች የሕዝብን ጥያቄና አቤቱታ በአግባብ ማስተናገድ ተፈጥሯቸው ስላልሆነ ሁልጊዜም ምላሻቸው ግድያና እስር መሆኑ ይታወቃል። በደቡብ ኢትዮጵያ ጎሙ ጎፋ ውስጥ የኮንሶ ሕዝብ ያቀረበው አስተዳደራዊ ጥያቄ የወያኔ አገዛዝ ግድያና በእስር ለማቆም ከሳምንታት ጀምሮ በግድያ የሰለጠነው ጦሩን በኮንሶ አስፍሮ ግድያ መፈጸሙ የሚታወቅ ሲሆን ይህ የሕዝብ ጥያቄና ተቃውሞ እንደገና ተቀስቅሶና አገርሽቶ በመነሳቱ የወያኔ መሪዎች የተመደውን የጥይት ምላሽ በመስጠታቸው ሶስት የኮንስ ነዋሪዎች መገዳላቸውና ሌሎቹ ደግሞ መቁሰላችው ተገልጿል። የወያኔ ነፋስ ገዳይ ጦርና የአካባቢዎች ፖሊስ የኮንሶ ከተማን በመክበብና በመውረር ነዋሪውን ጭንቀት ውስጥ እየተከቱትና ወታደራዊ ሽብርን በመላ ኮንሶ ለማድረስ ጥረት እያደረጉ መሆናችው ታውቋል። ከዚህ በተጨማሪ የወያኔ ጦርና የፖሊስ ኃይል የኮንሶ ከተማ ነዋሪን በግዳጅ የድጋፍ ሰልፉ እንዲያደርግ ቀስቀሳ መጀመራችው ታውቋል። በኮኖስና በአጎራባች ከተሞች ውጥረቱ ከፍተኛ ሲሆን የወያኔ ወታደሮች የሕዝብን ንብረት ዘርፈው እየወሰዱ መሆናቸው ተገልጿል። የፖሊትካ ታዛቢዎች የሕዝብን ጥያቄ በአግባብ መመለስ ብቻ የተቃውሞውን ጥያቄ የሚመልስ  ውጥረትን የሚያላላ መሆኑ ታውቆ እስካልተሰራበት ድረስ ወያኔ በኃይልና በግዳጁ ሊፈጽመው የሚችል አንዳች ነገር የለም በማለት አስተያየት ይሰጣሉ። 

Ø በናዝሬት የአዳማ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ተቃውሞ እንደገና የተቀስቀሰ ሲሆን ወያኔ አግአዚ ጦሩን በመላክ ተማሪዎቹ ን ሲደበድብ የቆየ ከመሆኑ በላይ በጅምላ ያሰራችው መሆኑ ታውቋል። ትናንት መጋቢት 5 ቀን 2008 ዓም ወደ አዳማ ዩኒቨርስቲ ዘልቆ የገባው የወያኔ አግአዚ ጦር ተማሪዎችን በማፈስ በናዝሬት ስታዲዮም እንዳሳደራቸው ሲታወቅ ምክንያቱ ባልታወቀ ሁኔታ የዩኒቨርስቲው የሠት ተማሪዎች መኝታ ክፍሎች በእሳት መቃጠላችውና ጉዳት እንደደረሰባችው ተገልጿል። በዛሬው ዕለት ተማሪዎቹችን ወደ አልታወቀ ቦታ ይዘዋወራሉ ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን ለተማሪዎቹ ምንም ዓይነት ምግብም ሆን ልብስ እንዳይገባላቸው ተከልክሏል። በአዳም ዩኒቨርስቲ ትምህር ሙሉ በሙሉ የተቋረጠ መሆኑም ከናዝሬት የተገኘው መረጃ ያመልክታል። የወያኔው ጠቅላይ ሚኒስተር ተብየው ለተፈጠረው ችግር ለጠፋው ህይወት ለፕሮፓጋንዳ ፍጆታ ብቻ ይቅርታ ይጠይቀ እንጅ በሕዝብ ልጆች ላይ የሚፈጸመው ግድያ እስርና ድብደባ ግን አሁንም እንዳልቆመሁሉ ህዝባዊ ተቃውሞና ቁጣውን በኃይልና በጭካኔ ለማቆም የተደረገው ሙከራ ውጤት አልባ መሆኑ ታይቷል።

Ø የአዋሳ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች በወያኔ ፖሊስ ከፍተኛ ድብደባ እንደተፈጸመባቸው የጅምላ አፈሳና እስር እንደተፈጸመባቸው ከአዋሳ የመጣው መረጃ ያለመክታል። እንደ መረጃው ከሆነ የአዋሳ ዩኒቨርስቲ ተማሪዎች መጋቢት 3 ቀን 2008 ዓ.ም. ማምሻውን ተደብደበውና ታስረው ንጋቱ ላይ በከባድ ካሚዮን ተጭነው ወደ አልታወቀ ቦታ መወሰዳቸውን አስረድቷል። ለተማሪዎቹ የጅምላ አፈሳና እስር ምክንያት የሆነው በአዋሳ ስታዲዮም ተዘጋጅቶ በነበረው የስፖርት ፌስቲቫል ላይ ተቃውሞ የቀሰቀሳችሁ እናንት ናችሁ በሚል ሲሆን የወያኔው አግአዚ ጦር በተማሪዎቹ ላይ በመኝታ ክፍሎቻቸው ሳይቀር በመግባት ድብደባ መፈጸሙንና አስሮ መውሰዱን ተብራርቷል። የአዋሳ ዩኒቨርስቲ ፕሬዚዳንት የተባለው ዮሴፍ ማሞ የወያኔን ጦር ወደ ዩኒቨርስቲ ግቢ በማስገባትና ተማሪዎችን በማስደብደብ አቢይ ሚና መጫወቱ ተደርሶበታል።
Ø  
Ø በሚቀጥለው እሁድ መጋቢት 11 ቀን  በናይጀር በሚደረገው የሁለተኛ ዙር ምርጫ የአሁኑ ፕሬዚዳንት የቅርብ ተፎካካሪ የነበሩት የተቃዋሚው ክፍል መሪ ሃማ አማዶ ከታሰሩበት እንዲፈቱ የቀረበውን ማመልከቻ አንድ የናይጀር የይግባኝ ፍርድ ቤት ሳይቀበለው ቀርቷል። ሃማ አማዶ ህጻናትን ህገ ወጥ በሆነ መንገድ አስተላልፈዋል በሚል ማስረጃ በሌለው ክስ ተጠርጥረው  ካለፈው ህዳር ወር ጀምሮ ታስረው የሚገኙ ሲሆን ከእስር ቤት ሆነው ባደረጉት ውድድር በመጀመሪያ ዙር በተደረገው ምርጫ 18 ከመቶ አግኝተው እንደነበር ተገልጿል። በመጀመሪያ ዙር ምርጫ አሁን በስልጣን ያሉት ፕሬዚዳንት ማሃማዱ ኢሱፉ (Mahamadou Issoufou) የምርጫውን 48 ከመቶ ብቻ በማግኘታቸው ምክንያት አሸናፊ ሆኖ ለመውጣት ያልቻሉ ሲሆን የተቃዋሚ ኃይሎች ምርጫው የተጭበረበረ ነው በማለት ክስ ማቅረባቸው ይታወቃል። በሃማ አማዶ ላይ  የቀረበውን ክስ አስመልቶ ፍርድ ቤት ቤቱ ሰኞ መጋቢት 5 ቀን 008 ዓም ውሳኔ መስጠት የነበረበት ሆኖ ሳለ የውሳኔውን ቀን ወደ መጋቢት 19 ቀን 2008 ዓም  በማስተላለፉ ምክንያት በውድድሩ ወቅት ሃማ አማዶ በእስር ቤት ሆነው መቆየት ግድ ሆኖባቸዋል። ጠበቆቻቸው በዋስ እንዲፈቱ ያቀረቡትን ማመልከቻ አልቀበልም ማለቱ እና የውሳኔውን ቀን ከምርጫው አንድ ሳምንት በኋላ ማስተላለፉ ፍርድ ቤቱ የአገዛዙ ተባባሪና ደጋፊ መሆኑን አሳይቷል የሚሉ ወገኖች በርካታ ናቸው።  

Ø አንድ የናይጄሪያ ፍርድ ቤት የናይጄሪያ የኢኮኖሚና የገንዘብ ወንጀል ለመመርመር የተቋቋመው ኮሚሽንና የወታደሩ ተቋም የሚከተሉት  የአምባገንነ አገዛዝ አሰራር ነው ካለ በኋላ በሙስና ወንጀል ተጠርጥሮ ተይዞ ክስ ሳይቀርብበት ከሶስት ወር በላይ በእስር ላይ የሚገኝ አንድ የኮሎኔል ማዕረግ ያለው ግለሰብ ባስቸኳይ እንዲፈታ ጠይቋል። ኮሎኔሉ ቀደም ብሎ 2.9 ሚሊዮን ዶላር በማጉደል በእስር ላይ የሚገኙት የቀድሞ የናይጄሪያ ወታደራዊ ተቋም አማካሪ የሚስተር ዳሱኪ ረዳት ሲሆን እስካሁን ክስ ያለተመሰረተበት መሆኑ ይታወቃል። ቀደም ብሎ ሚስተር ዳሱኪ ከእስር እንዲፈቱ ሶስት የተለያዩ ፍርድ ቤቶች  ውሳኔ ቢያስተላልፉም የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ግለስቡ በእስር እንዲቆዩ አዘዋል። አንዳንድ የህግ ሰዎች ፕሬዚዳንቱ በሙስና ስም የሚወስዱት እርምጃ የፖለቲካ በቀል ነው ሲሉ የሰብአዊ መብት ድርጅቶች ደግሞ ከመንግስት ባለስልጣኖች በተጨማሪም  ወታደሮቹም ሆኑ ዳኞች በሙስና የተጨማለቁ ናችው በማለት ይከሷቸዋል።
በተያያዘ ዜና የመንግስት ንብረት የሆነውና የናይጀሪ ናሽናል ፔትሮሊየም ኮርፖሬሽን (Nigeria National Petrolium Corporation) የሚባለው የናይጄሪያ ነዳጅ ድርጅት እንደ አውሮፓ አቆጣጠር በ2014 የበጀት አመት ወደ መንግስቱ ግምጃ ቤት ማስተላለፍ የነበረበትን 16 ቢሊዮን ዶላር ያላስገባ መሆኑ በምርመራ ተደርሶበታል። የዛሬ ሁለት ዓመት በቀድሞ የናይጄሪያ መንግስት አስተዳድር ወቅት ድርጅቱን ሲመሩ  የነበሩት ግለሰብ 20 ቢሊዮን ዶላር አጉድለዋል ተብለው መከሰሳቸው ይታወሳል። ናይጀሪያ በያመቱ በአማካይ 77 ቢሊዮን ዶላር የሚገመት ነዳጅ የምታመርት ስትሆን በርከት ያለው ገንዘብ በሙስና ይበዘበዛል ይባላል። 

Ø እሁድ መጋቢት 4 ቀን 2008 ዓ.ም. ራባት በሚባለው የሞሮኮ ዋና ከተማ ከአንድ ሚሊዮን በላይ የሆነ ሕዝብ ወደ አደባባይ ወጥቶ በቅርቡ የተመድ ዋና ጸሐፊ ባንኪ ሙን ስለምዕራብ ሳህራ ጉዳይ የሰጡትን አስተያየት አውግዟል። ዋና ጸሐፊው ሰኞ ዕለት ኒውዮርክ በሚገኘው በተመድ ጽሕፈት ቤታቸው የሞሮኮን አምባሳደር ጠርተው ባነጋገሩበት ወቅት በእሳቸው ላይ በሞሮኮ ባለስልጣኖች የተሰነዘሩት ስድቦችና ክሶች በጣም ያሳዘናቸውና ያበሳጫቸው መሆኑን ገልጸዋል ተብሏል።  ሕዝብ አደረገ በሚባለው ሰላማዊ ሰልፍ  የመንግስት ባለስልጣኖች መኖራቸውን አስመልክቶ ማብራሪያ እንዲሰጣቸው ጠይቀዋል ተብሏል። በማዕድን ሀብቷ የምትታወቀው የምዕራብ ሳህራ ግዛት በ 1967 ዓም ከስፔን ቅኝ ገዥነት ነጻ ስትወጣ ሞሮኮ በኃይል ወደ ግዛቷ በማጠቃለሏ ፖሊ ሳሪዮ በተባለው ድርጅት አማካይነት ለረጅም ዓመታት የትጥቅ ትግል  ሲካሄድ መቆየቱ ይታወቃል። በ1982 ዓም በተመድ አማካይነት በተጻራሪ ወገኖች መካከል ድርድር ተካሄዶ ጉዳዩን በውሳኔ ሕዝብ ለመጨረስ ስምምነት ቢደረግም የታቀደው ውሳኔ ሕዝብ እስካሁን አለመካሄዱ የተመድ ባለስልጣኖችን ሲያሳስብ ቆይቷል። ባለፈው ሳምንት ባንኪ ሙን በአልጀሪያ በካምፕ ውስጥ በስደት ላይ የሚገኙትን የምዕራብ ሳህራ ዜጎች  ሁኔታ አይተው አገርን በሃይል የመያዙ ሁኔታ አብቆቶ በስምምነት ስደተኞቹ ወደ አገራቸው መመለስ አለባችው የሚል ቃል በመናገራቸው የሞሮኮን ባለስልጣኖች ማበሳጨቱ  ይታወሳል። 

Ø ማይንማር ወይም በቀድሞ ስሟ በርማ የምትባለው አገር ላለፉት 50 ዓመታት በወታደራዊ አምባገነን አገዛዝ ስር ስትማቅቅ ቆይታ ለመጀመሪያ ጊዜ በምርጫ አዲስ ፕሬዚዳንት አግኝታለች።  ናሽናል ሊግ ፎር ዴሞክራሲ የተባለውን ፓርቲ በመወከል የተወዳደሩት ሂትን ኪያው ፕሬዚዳንት ሆነው ሲመረጡ እሳቸውም የታዋቂዋ የፖሊቲካ እንቅስቃሴ መሪ የኦንግ ሳን ሱ ኪ የቅርብ ረዳት ናቸው ተብሏል። ኮንግ ሳን ሱ ኪ የፓርቲው መሪ ቢሆኑም ከውጭ ዜጋ ወልደዋል በሚል ምክንያት በህገ መንግስቱ እንዳይወዳደሩ ቢከለሉም በፓርቲ መሪነታቸው ከጀርባ ሆነው የመንግስቱን ስራ ሊያካሂዱ እንደሚችሉ ገልጸዋል። 

No comments:

Post a Comment