Thursday, March 10, 2016

መንግስት እየጨመረ የመጣውን የማንነት ጥያቄ እንደማይቀበል ጠ/ሚኒስትሩ አስታወቁ

 አቶ ሃይለማርያም ደሳለኝ ዛሬ የመንግስትን የ6 ወር እቅድ ለፓርላማ ባቀረቡበት ወቅት እንዳመለከቱት፣የማንነት ጥያቄ እየጨመረ መምጣቱ፣ለመንግስት ችግር ፈጥሯል። ከእንግዲህ ወዲያ ጥያቄውን አናስተናግድም ሊባል እንደሚገባ ተናግረዋል። ጥያቄውን ይዘው በተነሱት ላይ ሁሉ እርምጃ እንደሚወሰድ ገልጸዋል።ጠ/ሚኒስትሩ በማንነት ዙሪያ ችግሮችና አፈታታቸው ላይ ሰጡት መልስ እርስ በርስ የሚጣረስና መንግስት የገባበትን አጣብቂኝ የሚያሳይ ነው። በሰሜን ጎንደር ዞን ከቅማንት ህዝብ ጥያቄ ጋር በተያያዘ በሰጡት መግለጫ፣ የማንነት ጥያቄ፣ ከመጀመሪያውም በህገመንግስት መልስ ያገኘ በመሆኑ የግጭት መንስኤ ሊሆን አይገባውም ነበር በማለት፣ ጥያቄውን ሲያጓትቱ የነበሩ ሃይሎችን ወቅስዋል።የብሄረሰብ ጥያቄ ምንም ችግር የማይፈጥር ለመሆኑ ታሪካችን ምስክር ነው ያሉት አቶ ሃይለማርያም፣ የቅማንትን ህዝብ ጥያቄ በማምታትና በፍጥነት በመመለስ ጉዳዮች ዙሪያ ችግሮች ነበሩ ብለዋል። አቶ ሃይለማርያም የህዝብን መብት የሚገድብ ህገ መንግስት የለንም ፣ የማንነት ጥያቄ የግጭት መንስኤ ሊሆን አይገባውም ብለዋል። አቶ ሃይለማርያም፣ የማንነት ጥያቄ የግጭት መንስኤ ሊሆን እንደማይገባውና ህገመንግስቱም የህዝብ መብት የሚገድብ አለመሆኑን ከተነጋሩ በሁዋላ፣ በደቡብ ክልል የሚታዩትን በርካታ የማንነት ጥያቄዎችን በተመለከተ ከቅማንት ጋር በተያያዘ ከተናገሩት ጋር ተቃራኒ የሆነ መልስ ሰጥተዋል። በደቡብ ክልል ያለው የማንነት ጥያቄ ፣ ህገመንግስቱ መልስ የሰጠ በመሆኑ፣ በየሰፈሩ የሚነሱ የማንነት ጥያቄዎችን አያስተናግድም ብለዋል። የፌደሬሽን ምክር ቤትና የብሄረሰብ ምክር ቤቶች ማንኛውንም የብሄረሰብ ጥያቄ ማስተናገድ አይገባቸውም ያሉት አቶ ሃይለማርያም፣ በንግግራቸው ቀደም ብለው "የህዝብን መብት የሚገድብ ህገመንግስት የለንም ፣ የብሄረሰብ ጥያቄ ምንም ችግር የማይፈጥር ለመሆኑ ታሪክ ምስክራችን ነው" በማለት ከተናገሩት ጋር የሚጣረስ መሆኑን ዘጋቢያችን ገልጿል ለቅማንት ህዝብ የተፈቀደው የማንነት ጥያቄ ለኮንሶ፣ ለቁጫ፣ ለሲዳማና ለሌሎችም ብሄረሰቦች ለምን እንደተከለከለ አቶ ሃይለማርያም ዝርዝር ማብራሪያ አልሰጡም። እንዲሁም ከወልቃይት ጠገዴ ጋር በተያያዘ ለተነሳው የማንነት ጥያቄ፣ አቶ ሃይለማርያም መልስ አልሰጡም።
የወልቃይት ጠገዴ ህዝብ የአማራ ብሄር ማንነት ጥያቄ በአገር ሽማግሌዎች እየተጠና መሆኑን የአማራ ክልል ፕ/ት አቶ ገዱ አንዳርጋቸው መገልጻቸው ይታወሳል። በተለያዩ የደቡብ ክልል የሚገኙ ብሄረሰቦች፣ "የቅማንትና የወልቃይት ጠገዴ የማንነት ጥያቄ እየተስተናገደ፣ የደቡብ ክልል ብሄረሰቦች የማንነት ጥያቄ ለምን በተመሳሳይ መንገድ አይሰተናገድም፣ በአንድ አገር ውስጥ ሁለት አይነት ህገመንግስት፣ ሁለት አይነት ዜግነት አለወይ ?" በማለት ጥያቄ ያቀርባሉ። አቶ ሃይለማርያም "ከእንግዲህ የማንነት ጥያቄ መስተናገድ የለበትም፣ ተመልሷል አልቋል" በማለት ለፌደሬሽን ምክር ቤት የሰጡት ትእዛዝ፣ የወልቃይት ጠገዴ ህዝብ ጥያቄ መፍትሄ ሳይሰጠው ባለበት እንዲቆም ለማድረግ" በህወሃቶች ግፊት የተናገሩት ሊሆን ይችላል በማለት ዘጋቢያችን ግምቱን አስፍሯል። በሌላ በኩል ደግሞ የኤሌክትሪክ መቆራረጡ ዋንኛው ምክንያት የሀይል ማመንጫዎች በሙሉ አቅማቸው መስራት ባለመቻላቸው መሆኑን ጠ/ሚኒስትሩ ለመጀመሪያ ጊዜ አምነዋል። አቶ ሃይለማርያም በሪፖርታቸው ከኤልኒኖ ክስተት ጋር ተያይዞ በቂ ውሀ ወደግድቦች ባለመግባቱ የተከዜ፣ የመልካወከና፣ የቆቃና የግልገል ጊቤ አንድ የሀይል ማመንጫ ጣቢያዎች ከአቅማቸው ከ10 በመቶ በታች እንደሚያመርቱ፣ አንዳንዶቹም ጨርሶ የማያመርቱበት ሁኔታ አጋጥሞአል ብለዋል። ሙሉ በሙሉ ሲጠናቀቅ 1870 ሜጋዋት ያመነጫል ተብሎ የሚታሰበው ግልገል ጊቤ ሶስት በአሁኑ ሰአት 540 ሜጋዋት ማመንጨት መጀመሩ መንግስታቸውን ከቀውስ እንዳዳነው ጠ/ሚኒስትሩ ተናግረዋል። በቀጣይ ጊቤ 3 ሙሉ በሙሉ ወደስራ ሲገባና የሌሎችም ግድቦች ማመንጨት ሲጀምሩ በሀይል አቅርቦት ምክንያት የደረሰብንን ጫና እንደሚቀንስ እምነት አለን ብለዋል። የግድቦቹ የሀይል ሁኔታ መሻሻል ሳያሳይ የሀይል መስመር የተዘረጋላቸው አንዳንድ የገጠር ማእከላትና ትንንሽ ከተሞች መብራት እንደማያገኙ ተናግረዋል። ባለፉት ሁለት አመታት የሀይል መቆራረጥ በየቀኑ በተደጋጋሚ ሲያጋጥም አቶ ሀ/ ማርያምን ጨምሮ ሌሎች ባለስልጣናት አንድ ጊዜ "የሀይል እጥረት የለብንም፣ የስርጭት ችግር ነው፣" ሌላ ጊዜ "ችግሩ የመልካም አሰተዳደር ነው፣ የኤሌክትሪል ሀይል ተሸካሚ መስመሮች እርጅና ነው" የሚሉ የተለያዩ ምክንያቶችን ለህዝብ ሲሰጡ ቆይተዋል። የኤሌክትሪክ ሀይል መቆራረጥ ችግር በተለይ ለውጭ ሀገር ገበያ ጭምር የሚያመርቱ ኢንዱስትሪዎች ከአቅማቸው በታች እንዲያመርቱና ሰራተኞች እንዲቀንሱ ያስገደደ ሲሆን፣ሌሎች እንደፖስታ፣ መኮረኒ፣ ዱቄትና የመሳሰሉ አምራች ፋብሪካዎች ምርታቸው ላይ ዋጋ ለመጨመር ተገደዋል።

No comments:

Post a Comment