Monday, April 11, 2016

ኢትዮ ቴሌኮም የሞባይል ቀፎዎችን ምዝገባ በሰራተኞቹ ንብረት ሊጀምር ነው

mobile(ሳተናው) ቀረጥ ሳይከፈልባቸው ወደ አገር ውስጥ የገቡ ሞባይልን ጨምሮ ተንቀሳቃሽ የቴሌኮም መገልገያ መሣሪያዎችን ከአገልግሎት ለማስወጣት የሚያስችለውን የመገልገያ ቁሶች ምዝገባ፣ ኢትዮ ቴሌኮም በቀጣዩ ሳምንት በሙከራ ደረጃ በሰራተኞቹ መገልገያዎች ላይ  ለመጀመር ዝግጅቱን ማጠናቀቁ ታውቋል ፡፡

ቴሌ ኮም የመገልገያ ቁሶቹን ምዝገባ የሚያከናውነውም ደንበኞቹ  ወደ ድርጅቱ ሳይሄዱ  ባሉበት  ቦታ ሆነው ነው ተብሏል፡፡ድርጅቱ ይህንን ለማድረግ የሚያስችለውን የመመዝገቢያ  ቴክኖሎጂ ከቱርክ የሶፍት ዌር ኩባንያዎች መሸመቱ ተነግሯል፡፡
ቴሌ ኮም የሚጠቀምበት ቴክኖሎጂ “Equipment Identity Registration (EIR)” የሚል መጠሪያ ያለው ሲሆን፣ ደንበኞች ሲም ካርድ በሚቀበሉ የመገልገያ ቁሶቻቸው ውስጥ የድርጅቱን ሲም ካርድ በከተቱበት ፍጥነት፣ የመገልገያ ቁሱን ዓይነትና መለያ ቁጥር ወደ ኢትዮ ቴሌኮም የመረጃ ቋት የሚያስገባ ቴክኖሎጂ ነው፡፡
በመሆኑም መረጃውን ከኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን መረጃ ጋር በማገናዘብ ቀረጥ ተከፍሎበት ወደ አገር ውስጥ የገባ ስለመሆኑ ማጣሪያ ከተደረገ በኋላ፣ ቀረጥ ያልከፈለ ሆኖ ከተገኘ ሲም ካርዱን መቆለፍና የመገልገያ ቁሱ የኢትዮ ቴሌኮምን ኔትወርክ እንዳይጠቀም ማድረግ የሚያስችለው ነው፡፡
በዚሁ መሠረት ኢትዮ ቴሌኮም ምዝገባውን በደንበኞቹ ላይ ከመጀመሩ አስቀድሞ፣ የራሱ ሠራተኞች የቴሌኮም አገልግሎት መቀበያ ቁሶችን ለመመዝገብ አቅዷል፡፡
የድርጅቱ ሰራተኞች እስከ መጪው ሚያዝያ 6 ቀን 2008 ዓ.ም. ድረስ ሞባይል፣ አይፓድ፣ ገመድ አልባ ዋይፋይ ራውተር፣ ታብሌቶችና ሌሎች ሲም ካርድ በሚቀበሉ መገልገያ መሣሪያዎቻቸው ውስጥ ሲም ካርድ ማኖር ይኖርባቸዋል፡፡
ቴክኖሎጂው ታክስ ሳይከፍሉ አገር ውስጥ የገቡ መገልገያዎችን ከመቆጣጠር በተጨማሪ፣ ተመሳስለው የተሠሩ ቀፎዎችን ከአገልግሎት ውጪ ለማድረግና የተሰረቁ ቀፎዎችን ይዘጋልም ተብሎለታል፡፡
ኢትዮ ቴሌኮም በአዲሱ የሞባይል ቀፎዎች ምዘገባ ዙሪያ ባሳለፍነው ዓርብ መጋቢት 30 ቀን 2008 ዓ.ም. ከመገናኛና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር፣  ከኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣንና ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በዝግ ውይይት ሲያደርግ እንደነበርም ለማወቅ ተችሏል፡፡
http://www.satenaw.com/amharic/archives/15266
ምንጭ ሪፖርተር

No comments:

Post a Comment