Monday, April 11, 2016

በቶሪኖ የተጠራው የመንግስት ስብሰባ በተቃውሞ ተበተነ

ሚያዚያ ፫( ሦስት) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- እሁድ ሚያዚያ 3፣ 2008 ዓም በጣሊያኑዋ የቶሪኖ ከተማ መንግስት ለአባይ ግድብ ማሰሪያ ቦንድ ለመጨጥ እንዲሁም አወዛጋቢ የሆነውን የኮንዶሚኒየም ሽያጭ ለማከናወን እና የውጭ ምንዛሬ ለመሰብሰብ የጠራው ስብሰባ በከተማዋ በሚገኙ ኢትጵያውያን ተቃውሞ እንዲሰረዝ ተደርጎአል፡፡ ኢትዮጵያውያኑ ገና ከመነሻው ተቃውሞአቸውን ያሰሙ ሲሆን፣ መሰረታዊ የሚባሉ የመብት፣ የእኩልነትና የኢኮኖሚ አስተዳደር ጥያቄዎችን አንስተው ተቃውአቸውን አሰምተዋል፡፡ አንድ አራተኛው የኢትዮጵያ ህዝብ በተራበበት ሁኔታ፣ ቅድሚያ የሰዎችን ህይወት መታደግ ሲገባችሁ እናንተ ግን የት እንደምታደርሱት ለማይታቅ ገንዘብ ለመሰብሰብ አጀንዳ ከፈታችሁ፤ ይሄ ከአገርም በላይ ሰብአዊነትን የሚመለከት በመሆኑ ቅድሚያ ለሰው ልጅ ህይወት ስጡ ያሉት ዜጎች፣ ከ300 በላይ የኦሮሞ ወገኖች ባለቁበት ሰአት፣ በሺዎች የሚቆጠሩ ታስረው በሚሰቃዩበት በዚህ ወቅት፣ እንዲሁም በወልቃይት ጥያቄ ዙሪያ ዜጎች ስቃያቸውን እያዩ፣ እናንተ ምንም ሳይመስላችሁ፣ ስለ ውጭ ምንዛሬ ልትነግሩን አጀንዳ ከፈታችሁ፣ ይሄ ያሳፍራል ሲሉ በምሬት ትቃውአቸውን ገልጸዋል፡፡ በውጭ ለሚገኘው ዜጋ ቤት ከመጨነቃችሁ በፊት በቅድሚያ ቤት አጥቶ ለሚሰቃየው አገር ቤት ላለው ህዝብ ቤት ስሩለት በማለት፣ በአገር ቤት ህዝብ ቤት አጥቶ እየተሰቃዬ፣ በተሻለ የኑሮ ሁኔታ ውስጥ ለሚገኘው በውጭ ለሚገኘው ዜጋ ቤት ለመስጠት የሚደረገውን ሩጫ በአስመሳይነት በመፈረጅ አውግዘዋል ኢትዮጵያውያኑበአገሪቱ ውስጥ የአንድ ብሄር የበላይነት መኖሩን፣ እንዲሁም ከ20 ሚሊዮን ህዝብ በላይ ተርቦ እናንተ ኢሳትን ለማፈን ከፍተኛ ገንዘብ ታወጣላችሁ በማለት የሞራል ጥያቄ አንስተው ተቃውመዋል፡፡ አገሩን ለቀን ወጣንላቸው ፣ እዚህ ደግሞ ገንዘባችንን ፡፡ ሊወስዱ ይመጣሉ በማለት ተቃውሞአቸውን በማሰማት መንግስት ስብሰባውን ለመሰረዝ ተገዱዋል፡፡ በፊላደልፊያም ተመሳሳይ ተቃውሞ መደረጉ ታውቆአል፡፡

No comments:

Post a Comment