Friday, April 29, 2016

የስራ ማቆም አድማና የተቃውሞ ሰልፍ ለማድረግ የጠየቁ የደሴ መምህራን እየተዋከቡ ነው ።


ሚያዚያ ፳፩(ሃያ አንድ) ቀን ፳፻፰ ዓ/ም ኢሳት ዜና :- ሚያዚያ 14፣ 2008 ዓም የደሴ ከተማ አስተዳደር መምህራን ማህበር አጠቃላይ 3ኛ ጉባኤ ተደርጓል። በስብሰባው ላይ የ33 ትምህርት ቤቶች የመሰረታዊ መምህራን ማህበር አመራሮች፣ የደሴ ከተማ ብአዴን ተወካይ፣ የትምህርት መምሪያ ሃላፊና የደህንነት ሰዎች ተገኝተዋል። የስብሰባው አጀንዳ የመምህራን ማህበር አመራሮችን ምርጫ ለማካሄድ ቢሆንም፣ ስብሰባው እንደተጀመረ መምህራን አሁን ስብሰባ ለማካሄድ አንችልም የሚል ተቃውሞ አሰምተዋል። የመምህራን መሰረታዊ ማህበራት አመራሮች ፣ “እኛ ከዚህ በሁዋላ ምርጫ አንፈልግም፣ ኢህአዴግ 25 አመታትን ገዝቷል፣ በቃው፣ ለውጥ አላየንም፣ ልማትና እድገት የለም፣ እኛ በረሃብ እየተሰቃየን ነው ፣ ማህበራችንን ማዋቀር አንፈልግም፣ ከፖለቲካ ነጻ አይደለም” ያሉ ሲሆን፣በተለይ መምህራን የትምህርት ጥራት እናስጠብቃለን እያልን ባለንበት ወቅት ትምህራታቸውን ያላጠናቀቁ መምህራን እየተመደቡ ዜጎቻችንን እያበላሹ በመሆኑ፣ ይህንንም እየተቃወምን ስለሆነ ህገመንግስታዊ መብታችንን ለማስጠበቅ ሰላማዊ እንቅስቃሴ እንደምናደርግ እናሳውቃለን ብለዋል። መምህራኑ ተቃውሞአቸውን ካቀረቡ በሁዋላ፣ በታዛቢነት የተገኙት የብአዴን ተወካይ፣ የትምህርት መምሪያ፣ የትምህርት መምሪያ ምክትል ሃላፊና ካድሬዎች የመምህሩን መብት በማፈንና በማስፈራራት ስብሰባውን እነሱ በሚፈልጉት መልኩ ለማስኬድ ጥረዋል። ባለስልጣናቱ ከፉከራ የዘለለ የምታመጡት የለም እንዳሉዋቸው የሚናገሩት መምህራን፣ ሰላማዊ ሰልፍም ሆነ የስራ ማቆም አድማ ማድረግ እንደማይችሉ ተናግረዋል። ከስብሰባው በሁዋላ አንድ የሁለተኛ ድረጃ ትምህርት ቤት የስራ ማቆም አድማ እንደሚያደርግ በመግለጽ ጽሁፍ ማቅረቡንም መምህራን ተናግረዋል። ይህን ተከትሎም በደሴ የጸጥታ ሃይሎች ከመቼውም ጊዜ በላይ ተመድበው ቅኝት በማድረግ ላይ ናቸው ፡፡ መምህራን ከኑኖረና ከአስተዳደር በደል ጋር በተያያዘ የተለያዩ ጥያቄዎችን በማቅረብ ላይ ሲሆኑ፣ መንግስት የጥያቄው መግፋት እያሳሰበው መምጣቱን ተከትሎ በቅርቡ ለመምህራን የቤትና የትራንስፖርት አገልግሎት እንደሚያመቻች ገልጿል።

No comments:

Post a Comment