Monday, July 25, 2016

(የአርበኞች ግንቦት 7 ድምፅ ሬዲዮ) ******************** የህዝብን ጥያቄ በጠብመንጃ ኃይል ጨፍልቆና አድበስብሶ ማለፍ አይቻልም፡፡ ********************




ደደቢት በረሃ ላይ እንደ አሸን የተፈለፈለው የህወሓት አገዛዝ ለህገ-አራዊት እየተመራ የኢትዮጵያን ህዝብ ላለፉት አመታት በመግደል፣ በማሰር፣ እንዲሁም የሃገርን ሃብት በመዝረፍ አስነዋሪ ወንጀል በመስራት ህዝቡንም በብሄርና በቋንቋ በመከፋፈል እንዲሁም ሃገርንም በክልልና በጎጥ በመሸንሸን ህብረተሰቡ ያለውን ኃይል እንዳይጠቀም በማድረግ ሰጥ ለጥ ብሎ እንዲገዛና አረመኔያዊ ስርዓት መውደቅ አለበት ብሎ በአደባባይ ወጥቶ በገሃድ እንዳይቃወም እግረ ሙቅ አስሮና አንገቱን አስደፍቶ እንዲኖር መፍረዱ ሳያንሰው በተለያ ጊዜ እራሱ በሚቆጣጠረውና እንደፈለገ በሚያሽከረክረው የቴሌቪዥንና የሬዲዮ ስርጭቱ ሃገራችን በእድገት ጎዳና ላይ በመገስገስ ላይ ትገኛለች፤ ህዝቡም የመብቱ ተጠቃሚ ሆኗል እያለ በተደጋጋሚ ጊዜ ሲዋሽ የቆየው የደደቢቱ አራዊት በአሁኑ ጊዜ በየአመቱ ተመዘገበ የሚባለው ባለሁለት አሃዝ የኢኮኖሚ እድገት ምናልባትም የህወሓት ባለስልጣናትና የእነሱ አጫፋሪ የሆኑ ጥቂት ግለሰቦችን ያካተተ ካልሆነ በስተቀር የኢትዮጵያ ህዝብ በአሁኑ ሰዓት የኑሮ ውድነት አንገሽግሾት የዴሞክራሲ እጦት አንገብግቦት ስርዓቱን በመቃወም በየአቅጣጫው ብሶቱን በማሰማት ላይ ይገኛል፡፡
እነዚህ የንፁሃን ደም ያሰከራቸውና ገና ወደፊትም በርካታ ንፁሃንን ደም ለመጠጣት በዝግጅት ላይ ያሉት የህወሓት ባለስልጣናት በተለያየ ጊዜ እነሱ እራሳቸው የስልጣን እድሜያቸውን ለማርዘም ሲሉ ብቻ ከህዝቡ የነጠቁትን ሰላም፣ ዴሞክራሲና ነፃነት ለማስመለስ በተለያዩ የሃገሪቱ ክፍሎች የሚደረጉ ህዝባዊ ተቃውሞዎችንም ሆነ ይህ ስርዓት ያንገፈገፋቸው የህዝብ ብሶት የወለዳቸው የኢትዮጵያ የቁርጥ ቀን ልጆች የሚያደርጉትን የትጥቅ ትግል ለማኮላሸትና ከህዝብ ለመነጠል ያልቆፈሩት ጉድጓድ ያልፈነቀሉት ድንጋይ የለም፡፡
ታዲያ የኢትዮጵያ ህዝብ አሁን በሚገኝበት ደረጃ ላይ ለመድረስ በወያኔዎችና በተላላኪዎች አማካኝነት ለበርካታ አመታት የሚያሰራጩለትን የሃሰት ወሬ አሜን ብሎ ሳይቀበለው ውስጥ ውስጡን በመደራጀትና የወያኔን እንቅስቃሴ በንቃት በመከታተል መብቱ ሲረገጥ፤ መሬቱ ሲነጠቅና የመኖር ህልውናው ሲጠፋ ዝም ብሎ ከማየት ይልቅ እስከ አፍንጫው የታጠቀውን የህወሓት አገዛዝ በትጥቅ ትግል በማንበርከክና ህዝቡንም የስልጣን ባለቤት ለማድረግ በሃገራችንም ሰላምና መረጋጋት እንዲሁም ዴሞክራሲያዊ የሆነ ስርዓት በመገንባት ወያኔ የከፋፈላትን ኢትዮጵያ ሳይሆን አዲሲቷን ኢትዮጵያ ለመገንባት ዱር ቤቴ ብለው ርሃብ፣ ውሃ ጥም፣ ሃሩርና ቁሩ ሳይበግራቸው ለዚህ ለተቀደሰ አላማ የሚታገሉ ሃይሎችን የተለያየ ታፔላ በመለጠፍና የተለያዩ ዘጋቢ ፊልሞችን በማዘጋጀት የህዝብን ይሁንታ ለማግኘትና የተጀመረው ትግል ተቀጣጥሎ ግቡን እንዳይመታ ለማድረግ በትጋት እየተንቀሳቀሰ የሚገኘው የዘመኑ ሰውበላና ጭራቅ የህወሓት አገዛዝ ባለስልጣናት ሰሞኑን እራሳቸው በሚቆጣጠሩት የቴሌቪዥን ስርጭት አስገራሚ ነገር ይዘው ብቅ በማለት የህዝብን የትኩረት አቅጣጫ ለማስቀየር ያደረጉት ሙከራ ሳይሳካ በመቅረቱ አሁንም ለሌላ የበቀል እርምጃ ህዝቡን እያመቻቹት ይገኛሉ፡፡
ከበርካታ ወራት በፊት ከፍተኛ የንብረት ውድመትና በርካታ የሰው ህይወት የጠፋበት የአዲስ አበባን ማስተር ፕላን በመቃወም በኦሮሚያ ክልል የተቀሰቀሰው ህዝባዊ ተቃውሞ እልባት ሳይገኝለት እስካሁንም ድረስ በተለያዩ ቦታዎች እየተቀጣጠለ ባለበት ሰዓት ይህንን የወያኔ የመሬት ሽንሸና እና ብሄርን ቋንቋን ብሎም ሃገርን የማጥፋት እቅዱን በመቃወም የወልቃይት ህዝብ የአማራ ማንነት ጥያቄን በማንሳቱና “የለም እናንተ አማራ አይደላችሁም መሬቱም የአማራ አይደለም” በማለት ከፍተኛ ብጥብጥና ሁከት በማስነሳቱ ምክንያት የወልቃይት ህዝብ ተሰብስቦ የራሱን የኮሚቴ አባላት መርጦ እስከ ፌደራል መንግስት ድረስ ሄደው ለጥያቄያቸው ምላሽ እንዲሰጣቸው ቢያደርጉም ወያኔዎች ግን ይህ የወልቃይት ህዝብ ጥያቄ ሳይሆን የአሸባሪዎችና የፀረ ሰላም ሃይሎች እጅ አለበት በማለት የኮሚቴ አባላቱን እና ንፁሃን ዜጎችን በማሰር ተቃውሞውን ለማቀዝቀዝ ሙከራ ቢያደርግም ጥያቄው የህዝብ ነውና ግጭቱ ወደለየለት ጦርነት ተቀይሮ ጎንደር ከተማን ጨምሮ ሽሬና ደባርቅ ከተሞች የጦር አውድማ ሆነው ሰንብተዋል፡፡
ታዲያ ወያኔዎች ይህ ሁሉ ሲሆን ሽንፈታቸውን ዝም ብለው ለመቀበል ፈቃደኛ አልሆኑም፡፡ ይልቁንም ጉዳዩ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ከሌላ ጋር ለማላተም ደፋቀና ሲሉ ሰነበቱ እንጂ፡፡
ሁል ጊዜም እንደሚያደርጉት ሁሉ ዛሬም የኢትዮጵያን ህዝብ ለማዘናጋትና ለመደለል ከየአቅጣጫው የተቀሰቀሰበትን ህዝባዊ አመፅለማብረድና በብልሃት አድበስብሶ ለማለፍ ያመቸው ዘንድ ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን ለማዳን የትጥቅ ትግል እያደረገ የሚገኘውን አርበኞች ግንቦት 7 ለአንድነትና ለዴሞክራሲ ንቅናቄ ከፍተኛ አመራሮች የስልክ ግንኙነት ሲያደርጉና ትግሉን ሲያቀጣጥሉ የሚያሳይ ተጨባጭ መረጃ አግኝቻለሁ በማለት ለህዝብ ጆሮ እንዲደርስ በማድረግና ሪፖርታዥ መግለጫ በማውጣት እንደለመደው ሲቀባጥር ታይቷል፡፡
ወያኔዎች በውስጥ የሚነሳባቸውን ህዝባዊ ተቃውሞ መቆጣጠር ሲሳናቸው ጉዳዩን ከሌላ ወገን ጋር በማዛመድ ያለ የሌለ እሮሮና ዛቻውን በማቅረብ በየቴሌቪዥን መስኮት ቀረርቷቸውን በመልቀቅ ያዙኝ ልቀቁኝ ሲሉ ይስተዋላሉ፡፡ ታዲያ ከሰሞኑም ወያኔዎች በመግለጫቸው ላይ ለመግለፅ እንደሞከሩት በብሄራዊ መረጃና ደህንነት እንዲሁም በፌደራል ፖሊስ አባላት ጥብቅ ክትትል የጎንደሩን ህዝባዊ አመፅ የመሩትና ህዝቡን የማደራጀት ስራውን ያከናወኑት የአርበኞች ግንቦት ሰባት አመራሮች ናቸው ቢሉም የሚያስገርም አይደለም ምክንያቱም እነሱ እንደሚያስቡት ሳይሆን የአርበኞች ግንቦት 7 ለአንድነትና ዴሞክራሲ ንቅናቄ ወያኔን በሚገባው ቋንቋ በመሳሪያ ትግል አምበርክኮ ለመጣል የሚያደርገው ትንቅንቅ እዛው ከህዝቡ ጎን በመሆን በሁለንተናዊ የትግል ስልት የታጀበና እስከ ነፃነት አደባባይ ድረስ የሚዘልቅ በመሆኑ ሁልጊዜም ቢሆን የኢትዮጵያ ህዝብ በወያኔ ባለስልጣናት የሚደርስበትን ስቃይና መከራ እያየ እጆቹን አጣጥፎ የሚቀመጥበት አንዳችም ምክንያት አለመኖሩን ጠንቅቀው ቢያውቁት በቴሌቪዥን መስኮት ብቅ ብለው ከደሙ ንፁነን በማለት የባጥ የቆጡን መዘላበድ አይጠበቅባቸውም ነበር፡፡ ነገር ግን ይህ ትግል የአርበኞች ግንቦት 7 ብቻ ሳይሆን የኢትዮጵያ ህዝብ ትግልም በመሆኑ አርበኞች ግንቦት 7 ለአንድነትና ዴሞክራሲ ንቅናቄ የሚያደርገው ትግል እንደመሆኑ መጠን እዛው ከኢትዮጵያ ህዝብ መካከል ሆኖ ለትግሉ አመቺ ናቸው ብሎ ያመነባቸውንና የወያኔን እድሜ ለማሳጠር ይበጁኛል ብሎ ለመጓዝ የቀየሳቸውን መንገዶች ለመከተል ትግሉን ከዚህም በበለጠ መልኩ ወደፊት የሚራመድበትን አቅጣጫ ነድፎ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል፡፡
ስለሆነም ህዝብ ሲበደል፤ ሲጨቆንና ሲሰቃይ፤ ህዝብ ሲገደልና ሲታሰር፤ ከጎኑ በመቆም የስቃዩ ተካፋይ ሆኖ መገኘት ሌላ ትርጉም የሚያሰጥ ሳይሆን ለወገን ደራሽ ወገን መሆኑን ወያኔዎች ቢያውቁት ፈጥነው ከህዝቡ የተነሳባቸውን የማንነት ጥያቄም ሆነ አስተዳደራዊ በደል ምላሽ ለመስጠት ቢጥሩ የተሸለ ነበር፡፡
እራሳቸው በፈጠሩት ትርምስና አላሰስፈላጊ እርምጃ ህዝብንና ለነፃነት የሚደረገውን የትጥቅ ትግል ለመነጠል ታስቦ የጎንደሩን ሁከትና ብጥብጥ ያስነሳው አርበኞች ግንቦት 7 ነው ለዚህም ማሳያው የስልክ ግንኙነት ሲያደርጉ የብሄራዊ መረጃና ደህንነት እንዲሁም የፌደራል ፖሊስ ስልኩን በመጥለፍ ተጨባጭ መረጃ አግኝቷል በማለት ጉራቸውን ሲቸረችሩ ሰንብተዋል፡፡
ወያኔዎች አርበኞች ግንቦት 7 በመላ ሃገሪቱ ህዝቡ መሃል ገብቶ ትግሉን እያጧጧፈው መሆኑን መረዳት አለመቻላቸው ብቻ ነው የሚያስገርመው፡፡ ይህንን የሰሞኑን የጎንደሩን ሁከትና ብጥብጥ የመሩት የአርበኞች ግንቦት 7 ከፍተኛ አመራሮች ናቸው በማለት ለህዝብ ይፋ ቢያደርጉም ህዝቡ ጆሮውን ሰጥቶ ሊሰማቸው አልቻለም፡፡ ምክንያቱም የኢትዮጵያ ህዝብ አርበኞች ግንቦት 7 ለአንድነትና ዴሞክራሲ ንቅናቄ ሁልጊዜም ቢሆን ትግሉን የሚያደርገው ከመካከላቸው በመገኘት ከህዝቡ በፊት እኔ ልቅደም በማለት የህይወት መሰዋትነት በመክፈል አጋርነቱን በቁርጠኝነት እያሳየ መሆኑን ጠንቅቆ ስለሚያውቅ ብቻ ነው፡፡
ወያኔዎች ታዲያ ይህንን ሽንፈታቸውን ዝም ብለው ለመቀበልና የህዝቡን ብሶት ሰምቶ ምላሽ ከመስጠት ይልቅ “የራሷ አሮባት የጎረቤት ታማስላለች” እንደሚባለው የራሳቸው ስህተት ከሌሎች ጋራ ሊያዛምዱ ሲውተረተሩ ከመታየታቸውም በላይ የኢትዮጵያን ህዝብ በመግደልና ደሙን አፍስሰው በመጠጣት ሃገርንና ህዝብን የማጥፋት ህልማቸውን እውን ለማድረግና ለማሳካት ለዳግም የበቀል እርምጃ እያመቻቹት ይገኛሉ፡፡
ታዲያ ወገን! ከወያኔ በላይ አሸባሪ ቡድን አለን? 
ለዚህም እንደ ዋንኛ ምክንያት ልንጠቅሰው የምንችለው ነገር ቢኖር በታጠቀው የጦር መሳሪያ ተኩሶ እንዲገድል ቀጥተኛ ትዕዛዝ በመስጠትና ግንባር ግንባራቸውን ብሎ በግፍ እናቱን፣ አባቱን፣ እህቱን፣ ወንድሙንና ዘመድ አዝማዱን እንዲጨፈጭፍ የሚያደርገው ማነው? ወያኔ አይደለምን? ከዚህ በላይ ምን ማረጋገጫ መስጠት ያስፈልገናል፡፡
በቅርቡ በወያኔዎች መንደር የተከሰተው የማደናበሪያ ስሜት የወልቃይት ህዝብ የአማራ ማንነት ጥያቄ የህዝቡ ጥያቄ ሆኖ ሳለ ወያኔዎች ግን ለዚህ አሳማኝ ለሆነ ጥያቄ መልስ ከመስጠት ይልቅ በጠብመንጃ ሃይል ለመጨፍለቅና የንፁሃንን ደም በከንቱ ለማፍሰስ ተፍተፍ በማለት ሲባዝኑ ቆይተው ህዝብ ቁጣ እረፍት ሲነሳቸው ጊዜ ይህ ህዝባዊ አመፅ የህዝቡ ጥያቄ ሳይሆን የፀረ ሰላም ሃይሎችና የአሸባሪዎች እጅ አለበት በማለት የህዝቡን ትኩረት አቅጣጫ ለማስቀየር ቢሞክሩም አሸባሪው እራሱ ወያኔ መሆኑን ህብረተሰቡ ተገንዝቦና በደንብ ተረድቶ ከፍተኛ የፖለቲካ ኪሳራ እንዲደርስበት አድርገውታል፡፡
ታዲያ የራሷ አሮባት የሰው ታማስላለች የሚለው አባባል ወያኔን አይገልፅም ትላላችሁ?

No comments:

Post a Comment