Sunday, January 29, 2017

ለቅሶህም ለቅሶዬ ነው ! ======//========


No automatic alt text available.መግቢያ፡ በየሣምንቱ ቅዳሜ በንቃት ከማዳምጣቸው የሬዲዮ አገልግሎት ሥርጭቶች አንዱና ዋነኛው በሻለቃ አብረሃም ታከለ አዘጋጅነትና አቅራቢነት የሚሰራጨውን የሠራዊቱ ድምፅ ነው ። ለምን ? ይህ ሬዲዮ የእኔና እኔን የመሰሉ የቀድሞው ሠራዊት አባል ልጆች ድምፅም ጭምር በመሆኑ ነው። ስለ ሠራዊቱም መስዋዕትነትና ተጋድሎ ሆነ ስለ ቤተሰቡ ሁኔታ በተጨባጭ ይናገራል። ሥርጭቱን ያላዳመጥኩበት ጊዜ የለም ብል አዘጋጁ ሊኮንነኝ ይችላል ። እ አ አ በወርሃ ጥቅምት መጀመሪያው ሣምንት 2014 እኔም የሬዲዮኑ የሠራዊቱ ቤተሰብ እንግዳ ሆኜ ቃለ መጠይቅ ሰጥቻለሁና ።

በጥር ፳ ቀን፳፻፱ ዓም አዘጋጁ ያቀረበው የቀድሞ ሠራዊት ቤተሰብ ልጅ የባሻው ግርማ ልጅ አቶ ታደሠ በቃለ መጠይቁ ወቅት ይሰጥ የነበረው በሳግና በለቅሶ የታጀበ መልስ ግን የሚያዳምጠውን በሙሉ መንፈስ የሚረብሽ ስለመሆኑ ለአፍታ አልጠራጠርም ። ምንአልባትም በዓለማችን ማን ያውቃል በሬዲዮን የቃለ ምልልስ ወቅት በረዠሙ የፈሰሱ እንባዎችና ሳግ የተቀላቀለባቸው ሊሆኑ ይችላሉ ። መቼስ ሰው ነኝና እኔም ተከፋሁ ተረበሹኩኝ ። ቀጥታ ላፕ ቶፑን ከፈትኩና በደሉን በቃላት ልጋራው ብዬ ይህችን የግጥም ስንኝ በችኮላም ቢሆን ደረደርኩኝ። ገና ጆሮ አይሰማው የለ ! ስንት በደል ፤ስንት ግፍ ፤ ስንት ጭካኔ ! ዕድሜ ይስጠን ብቻ !
እንጉርጉሮ !
=======

ሳግም ሲቃ ይዞን ፤ ዛሬም እናለቅሳለን
ክብርና ማዕረጉን፤ በባለቀኖቹ ለተገፈፈብን
ለቀድሞው ሠራዊት ፤ ወድቆ ለቀረብን
ማንም ያልደፈረው ፤ መከላከያችን
ድንበሩን ጠብቆ ፤ አጥሩን አጥብቆ
ባዕድ ጠላቶቹን ፤ በንቃት ጠብቆ
የኖረው ሠራዊት ፤ ተከብሮ ተደንቆ
ምስቅልቅሉ ወጣ ፤ ጥላሸት ተቀብቶ
በአገር አፍራሾቹ ፤ በመሰሪዎቹ ፤እንዳይሆን ተንቆ ።
ሻምበል ሥራ በቃ ፤ ወቴ ብላ ጠጣ
ግዳጅ ሊፈጽም ነው ፤ ሠራዊቱ መጣ።
ብለን እንዳልጨፈርን ፤ በሜዳ ጨዋታ
ቀውሱን ተጋራነው ፤ ልጆቹም በተርታ።
ሃዘን አኮራምቶን፤ ተርበን ታርዘን
መኖሪያ ቤት አጥተን፤ ቀያችንን ትተን
በደል ሲበዛብን ፤ ኑሮው ምርር ሲለን
ተበታትነን ቀረን፤ ልጅነት ሳያምረን
ሥራ ሠርተን መኖር፤ መታገል ጀመርን
አሳዳጊ አጥተን ፤ የሚንከባከበን 
ተስፋችን ጨልሞ ፤ በልጅነታችን
ኑሮውን ገፋነው ፤ እንዳይሆኑ ሆነን።
አይዟችሁ እደጉ ፤ ግቡ ትምህርታችሁ
የነገዋ ኢትዮጵያ ፤ ተስፋ ልጆች ናችሁ።
የሚለን ሰው ጠፍቶ ፤ የሚያበረታታን
ኖርናት ስናለቅስ ፤ የልጅ ዕንባ አፍሰን
ሳናየው በናፍቆት ፤ ፎቶ ብቻ እያየን
ወታደሩ አባባን ፤ የኛው መመኪያችን
ለሃገሩ ግዳጅ ፤ በሞት ለተለየን
የወደቀበትን ፤ መቃብሩን እንኳን
ሳናውቅ እ ን ኖ ራ ለ ን !
ወታደሩ አባባ ፤ እንወድሃለን፤ እንዘክርሃለን !

መታሰቢያነቱ ለሁሉም የቀድሞው መከላከያ ሠራዊትና የፖሊስ ሠራዊት አባላትና ቤተሰቦቻቸው ይሁን !
ሠሎሞን ታምሩ ዓየለ
ጥር ፳ ቀን ፳፻፱ ዓም

No comments:

Post a Comment