Monday, January 9, 2017

ህወሃት መራሹ አገዛዝ በንግድና ኢንዱስትሪ የተሰማሩ ባለሃብቶችን ከጎኑ ለማሰለፍ እያደረገ ያለው ሙራ እንዳልተሳካ ሾልከው የወጡ መረጃዎች አመለከቱ

ቀደም ሲል በመንግሥት ይዞታ ሥር ይተዳደሩ የነበሩ የንግድ ድርጅቶችን፤ ሆቴሎችንና  ኢንዱስትሪዎችን ወደ ግል ይዞታ ለመለወጥ ህወሃት እርምጃ በወሰደበት ወቅት ድርጅቶቹን በመግዛት ተጠቃሚ የሆኑ ባላሃብቶች የተሳተፉበት ስብሰባ ባለፈው ሳምንት አዲስ አበባ ውስጥ ተደርጎ እንደነበር በመንግሥት መገናኛ ብዙሃን የተገለጸበት ሁኔታና በስብሰባው ላይ የተንጸባረቁ አስተያየቶች የማይገናኙ እንደነበር እንድ ስማቸው እንዳይገለጽ የፈለጉ የስብሰባው ተሳታፊ  ለዝግጅት ክፍላችን ገልጸዋል።http://amharic.abbaymedia.com/%E
እንደ ተሳታፊው ገለጻ መንግሥት ይህንን ስብሰባ
የጠራው በመላው አገሪቱ ውስጥ ከጊዜ ወደጊዜ እያየለ የመጣውን ህዝባዊ ተቃውሞ ለማለሳለስ በንግዱ ዘርፍ ተሰማርተው የሚገኙ ባለሃብቶች ከመንግሥት ጎን ቆመው ያደረጉት አስተዋጾ ስለሌለ ለመውቀስና ውለታ የዋለላቸው መንግሥት በህዝብ ተቃውሞ ሲናጥ ዝም ብሎ መመልከት የኋላ ኋላ የእነርሱንም ጥቅም ሊጎዳ እንደሚችል በማስጠንቀቅ ድጋፋቸውን እንዲቸሩ ለማሳሰብ ነበር።  በስብሰባው ላይ የተገኙት የኢንቬስትመንት ቢሮ ከፍተኛ ባለሥልጣን ለተሰብሳቢው ባደረጉት ንግግር የኢህአደግ መንግሥት ሥልጣን ከተቆጣጠረበት ማግሥት ጀምሮ ባለሃብቶችን ለማፍራት ባደረገው እንቅስቃሴ በህዝብና በመንግሥት ቁጥጥር ሥር የነበሩ ትርፋማ ድርጅቶችን ወደ ግል ካዞረላችሁ ከናንተ በተለያየ ንግድ ከተሰማራችሁ ዜጎች የበለጠ የተጠቀመ ሰው በአገሪቱ የለም ማለታቸው በርካቶችን እንዳስቀየመ ተገልጿል። መንግሥት በአገሪቱ ውስጥ የተከሰተውን እንቅስቃሴ ለመቆጣጠር ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ላይ በሚገኝበት በዚህን ሰዓት እያንዳንዱ ባለሃብት ህብረተሰቡ ከመንግሥት ጋር እንዲቆም የተቻለውን ጥረት ማሳየትና ወገንተኝነቱን  መግለጽ ይኖርበታል በማለት ያሳሰቡት የኢንቬስትመንት ቢሮ ሃላፊ የመንግሥት ህልውናና የባለ ሃብቶች የንብረት ዋስትና የተያያዘ መሆኑን ለማሳመን ሙከራ አድርገዋል። ከዚህም በተጨማሪ በርካታ የአገሪቱ ወጣቶች በሥራ አጥነት ምክንያት ተስፋ ቆርጠው ባለሥልጣኑ ” ጸረ ሠላም”  ያሏዋቸው ሃይሎች መሣሪያ እየሆኑ ስለሆነ እያንዳንዱ ባለሃብት የሥራ ዕድል በመፍጠር የሥራ አጥ ወጣቶችን ቁጥር በመቀነስ መንግሥት ሠላምና መረጋጋትን ለመመለስ እያደረገ ያለውን ትግል እንዲያግዙ አሳስበዋል ተብሎአል።
ተሰብሳቢ ባለሃብቶች በበኩላቸው በየእርከኑ ያሉ የመንግሥትና የክልል ባለሥልጣናት ሲፈጥሩባቸው በኖሩ ተከታታይ አስተዳደራዊ እንቅፋቶች ምክንያት ኢንቬስትመንቶቻቸውን ማሳደግ ቀርቶ ባሉበት ይዞታ እንኳ ይዞ ለመቀጠል ሲቸገሩ እንደኖሩ በተደጋጋሚ አመልክተው ሰሚ እንዳጡ ቅሬታቸውን አምርረው ገልጸዋል። በመንግሥታዊ መዋቅር ውስጥ ተንሰራፍቶ የሚገኘው አድሎአዊ አሰራርና ሙስና ከፍተኛ የሆነ ማነቆ እንደሆነባቸው በምሬት የገለጹ እነዚህ ባለሃብቶች በተለይ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በአገሪቱ ውስጥ እየተካሄደ ያለው የተቃውሞ እንቅስቃሴ በፈጠረው ስጋት ምክንያት የንግድና ኢንቨስትመንት እንቅስቃሴያቸው ሙሉ በሙሉ በመዳከሙ የሠራተኛ ደመወዝና የመንግሥት ግብር እንኳ ለመክፈል ከማይችሉበት ደረጃ ላይ መድረሳቸውን ፊት ለፊት በመግለጽ ከመንግሥት ተልኮ የመጡትን ሰብሳቢዎች አስደንግጠዋል። በዚህም የተነሳ የንግዱን ማህበረሰብ ልዩ ተጠቃሚ ሆናችኋልና ከመንግሥት ጎን ቁም ለማለት ተልከው የመጡ የስብሰባው መሪዎች በጎዳና ላይ ወጥቶ ተቃውሞ እያሰማ ካለው ማህበረሰብ ያልተናነሰ ብሶትና ተቃውሞ ከተሰብሳቢው በመሰማታቸው ከበላይ አለቆቻቸው ጋር ተወያይተው ሌላ ስብሰባ ለመጥራት ቃል በመግባት ስብሰባውን  ያለውጤት ዘግተዋል እንደምንጫችን መረጃ።
በመንግሥት ቁጥጥር ሥር የሚገኙ የአገር ውስጥ መገናኛ ብዙሃን በስብሰባው ላይ የተንሸራሸሩ ሃሳቦችንና የመንግሥት ባለሥልጣናትን አስደንግጦ ያወጣውን ብሶት በመሸሸግ ባለሃብቶች ከመንግሥታቸው ጎን ቆመው ጸረ ሰላም ሃይሎችን እንደሚያወግዙ የሚያስመስል ዘገባ ማሰማታቸው ተጨማሪ ትዝብት ላይ ጥሎአቸዋል። አዲሱ የኮሚንኬሽን ምንስትር ዶር ነገሪ ሌንጮ በቅርቡ ከአዲስ ዘመን ጋር አድርገውት በነበረው ቃለመጠይቅ የመንግሥት ጋዜጠኞች እራሳቸውን ነጻ በማውጣት እውነትን እንዲዘግቡ አሳስበው እንደበር መዘገባችን ይታወሳል።

No comments:

Post a Comment