Thursday, July 7, 2016

(የአርበኞች ግንቦት 7 ድምፅ ሬድዮ)




በምዕራብ አርማጭሆ ወረዳ በተለምዶ ስሙ ስናር ከተባለው የእርሻ ቦታ በኢትዮጵያ ባለሃብቶችና በሱዳን የመከላከያ ሰራዊት መካከል ባለፈው ሰኔ 26 ቀን 2008 ዓ.ም. ለ 4 ሰዓታት ያህል የቆየ ውጊያ የተካሄደ ሲሆን የጦርነቱ መንስዔ የሱዳን ወታደሮች ድንበር ጥሰው ተሻግረው የኢትዮጵያን ባለሃብቶች ካምፕ በማቃጠላቸው በአካባቢው የሚገኙትና ካምፓቸው የተቃጠለባቸው ባለሃብቶች ባለ መሳሪያ በመሆናቸው ውጊያው ከጠዋቱ 1 ሰዓት ጀምሮ እስከ 4 ሰዓት የቆየ መሆኑን ከስፍራው የደረሰን መረጃ ይጠቁማል፡፡ በዚህ ውጊያም በሱዳን ወታደሮች በኩል 5 የሞተና ከዚያም በላይ የቆሰለ እንዳለ ለማወቅ የተቻለ ሲሆን ከኢትዮጵያ ባለሃብቶች ጌታው ጎዳና የተባለ ግለሰብ በውጊያው መሞቱ ታውቋል፡፡
በሱዳን ወታደሮች ካምፓቸው የተቃጠለባቸው ኢትዮጲያዊ ባለሃብቶች ብዙ ሲሆኑ ከነዚህም መካከል አበበች እና አሻገረ ባየሁ የተባሉ ባለሃብቶች ይገኙበታል፡፡ ለ 4 ሰዓታት ያህል የቆየው ውጊያ ከተጠናቀቀ በኋላ የወያኔ የመከላከያ ሰራዊት ከስፍራው ቢደርስም በሱዳን የመከላከያ ሰራዊት ላይ እርምጃ ከመውሰድ ይልቅ በባለሃብቶች የቆሰለውንና የተገደለውን የሱዳን የመከላከያ ሰራዊት ወደ ሱዳን ሲሸኝ መዋሉን መረጃው ጨምሮ ገልጷል፡፡
የወያኔ ቡድን ከዚህ በፊት ለሱዳን መንግስት በአካባቢው መሬት ቆርሶ የሰጠ ሲሆን አሁንም በዚህ ግጭት ላይ ከህዝብ ጎን መሰለፍ ቀርቶ ከሱዳን ሰራዊት ጋር የወገነ መሆኑ ወያኔ ለኢትዮጵያ ህዝብ ደንታ እንደሌለው የሚያመላክት ነው ተብሏል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ የወልቃይት የማንነት ጥያቄ ተባብሶ በመቀጠል ገሚሱ ወደ በረሃ ሲወጣ በቀሪው ህብረተሰብ ላይ ደግሞ እስርና ወከባው በወልቃይት ህዝብ ላይ ተጠናክሮ መቀጠሉን ለማወቅ ተችሏል ፡፡

No comments:

Post a Comment