Tuesday, May 10, 2016

በአርባ ምንጭ ያልታወቁ ሃይሎች የፖሊስ አባላትን ገደሉ



ኢሳት (ግንቦት 2 ፥ 2008) በአርባ ምንጭ ነጭ ሳር ፓርት አካባቢ ያልታወቁ ሃይሎች ከመንግስት ሃይሎች ጋር ባደረጉት ግጭት ቁጥራቸው ያልተገለጸ የፖሊስ አባላት ሲገደሉ፣ ከጣታቂዎች ወገን እንግዳ አበበ የተባለ ወጣት መገደሉን የአካባቢ ምንጮች ለኢሳት ገለጹ። በርካታ የፌዴራል ፖሊሶች ለህክምና ሆስፒታል መግባታቸው የተገለጸ ሲሆን፣ በከተማዋ የቤት ለቤት አሰሳ መቀጠሉም መረዳት ተችሏል። ቅዳሜ ሚያዚያ 29 ፥ 2008 ነጭ ሳር ብሄራዊ ፓርት አካባቢ በፌዴራል ፖሊሶች ላይ ድንገተኛ ጥቃት የሰነዘሩት የታጠቁ ሃይሎች፣ የአካባቢውን የፌዴራል ፖሊስ አዛዥና ቁጥራቸው ያልታወቀ ሌሎች የፌዴራል ፖሊስ አባላትን መግደላቸውን የሚገልጹት የኢሳት ምንጮች ከጥቃቱ ቀደም ባሉት ቀናትም በከተማዋ አሰሳ ሲካሄድ መቆየቱን አስታውሰዋል። በተለይ ሚያዚያ 27 ፥ 2008 ከምሽቱ 4 ሰዓት ጀምሮ በከተማዋ በተካሄደው አሰሳ አንዲት አራስን ጨምሮ 13 የከተማዋ ነዋሪዎች የታሰሩ ሲሆን፣ ከአርባ ምንጭ ተወስደው አዲስ አበባ በእስር ላይ የሚገኙት የአቶ ሉሉ መሰለ የ17 አመት ልጅም ከታሳሪዎቹ ውስጥ እንደሚገኝበትም የመጣው ዜና ያስረዳል። በሳምንቱ መጨረሻ በነጭ ሳር ፓርክ አካባቢ ከፌዴራል ፖሊስ ሃይል ጋር ግጭት ውስጥ የገቡት ታጣቂዎች ከየት የመጡና ዓላማቸው ምን እንደሆነ በግልፅ የተገለፀ ነገር ባይኖርም፣ በአካባቢው ነዋሪዎች ዘንድ የአርበኞች ግንቦት 7 ናቸው እየተባሉ እንደሚጠቀሱም ተመልክቷል።

No comments:

Post a Comment