Wednesday, October 28, 2015

ፍርድ ቤቱ በአቶ አንዳርጋቸው ጉዳይ ለሶስት አካላት ትዕዛዝ እንዲሰጥ ተጠየቀ በነገረ ኢትዮጵያ ሪፖርተር


በእነ ዘመነ ካሴ የክስ መዝገብ ከ2ኛ -5ኛ መዝገብ ለተከሰሱት አቶ አሸናፊ አካሉ (2ኛ ተከሳሽ)፣ አቶ ደናሁን ቤዛ (3ኛ ተከሳሽ)፣ አቶ ምንዳዬ ጥላሁን (4ኛ ተከሳሽ) እና አቶ አንሙት የኔዋስ (5ኛ ተከሳሽ) በመከላከያ ምስክርነት ተጠቅሰው በነበሩት አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ጉዳይ የልደታ ፍርድ ቤት 19ኛው ወንጀል ችሎት ለሶስት አካላት ትዕዛዝ እንዲሰጥ ተጠየቀ፡፡ የቃሊቲ ማረሚያ ቤት ጥቅምት 12/2008 ዓ.ም አቶ አንዳርጋቸው እሱ ጋር እንደሌሉ ለፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛው ወንጀል ችሎት በላከው ደብዳቤ መግለፁ ይታወሳል፡፡
ከ6ኛ-9ኛ ያሉት ተከሳሾች ማረሚያ ቤቱ በፈጠረው ችግር የአቶ አንዳርጋቸውን ምስክርነት ለመስማት የፍርድ ሂደታቸው እየተጓተተባቸው በመሆኑ የአቶ አንዳርጋቸው ምስክርነት ቀርቶ ብይን እንዲሰጥላቸው ሲጠይቁ 4ኛ ተከሳሽ አቶ ምንዳዬ ጥላሁን ‹‹ከአንዳርጋቸው ጋር ተገናኝተህ መመሪያ ተቀብለሃል ስለተባልኩ አቶ አንዳርጋቸው መጥቶ መመስከር አለበት›› ሲል አሁንም አቶ አንዳርጋቸው እንዲቀርቡለት ጥያቄውን አቅርቦ ነበር፡፡ ከአቶ ምንዳዬ ጥላሁን በተጨማሪ 3ኛ ተከሳሽ አቶ ደናሁን ቤዛም አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ እንዲመሰክሩለት በመፈለጉ፤ እና ፍርድ ቤቱም አቶ አንዳርጋቸው ይገኙበታል ተብሎ ለታሰበው ተቋም ትዕዛዝ ለመስጠት እንዲመቸው ተከሳሾቹ እንዲጠቁሙት በገለፀው መሰረት ተከሳሾቹ ፍርድ ቤቱ ለሶስት ተቋማት ትዕዛዝ እንዲሰጥላቸው በደብዳቤ ጠይቀዋል፡፡

ሁለቱ ተከሳሾች ጥቅምት 15/2008 ዓ.ም ለፌደራል ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 19ኛ ወንጀል ችሎት በፃፉት ደብዳቤ የፀረ ሽብር ግብረ ኃይል አቶ አንዳርጋቸው ፅጌን መያዙን በኢትዮጵያ ብሮድካስቲንክ ኮርፖሬት መግለጫ መስጠቱን፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማሪያም ደሳለኝ መስከረም ወር 2007 ዓ.ም የአቶ አንዳርጋቸው ፅጌን መያዝ፣ የእድሜ ልክና የሞት ፍርደኛ መሆናቸውን በመግለፅ የኢትዮጵያ መንግስት ፍርዱን ተፈፃሚ እንደሚያደርግ መግለፃቸውን አስታውሰዋል፡፡ በተጨማሪም በኢትዮጵያ የእንግሊዝ ኤምባሲ አቶ አንዳርጋቸው ዜግነታቸው እንግሊዛዊ የሆሉትን አቶ አንዳጋቸው ጉዳይ ላይ ክትትል እንደሚያደርግ በደብዳቤው አስታወስዋል፡፡
በመሆኑም ከእነዚህ ሶስት አካላት በላይ አንዳርጋቸው ፅጌ ስላሉበት ቦታ የሚያውቅ ስለሌለ ለሶስቱም አካላት አቶ አንዳርጋቸው የት እንዳሉ እንዲገልፁና አቶ አንዳርጋቸውም ምስክር እንዲሆኑላቸው ፍርድ ቤቱ ትዕዛዝ እንዲሰጥ ጠይቀዋል፡፡

No comments:

Post a Comment